Tuesday, July 9, 2013

አንዱአለምና ጋዜጠኛ እስክንድር ለኢትዮጵያ ህዝብ መልዕክት አስተላለፉ

የአንድነት ፓርቲ የህዝባዊ ንቅናቄ ግብረሀይል፣ የሶሻል ሚዲያ ኮሚቴ አባላት የነፃነት ታጋዮቹን አንዱአለም አራጌንና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ጎበኙ፡፡ የሶሻል ሚዲያ አባላቱ ትላንት በቃሊቲ እስር ቤት ባደረጉት ቆይታ የአንዱአለም እና የእስክንድር መንፈሳዊ ጥንካሬ እንዳስደሰታቸው ለፍኖተ ነፃነት ተናግረዋል፡፡

በጉብኝቱ ወቅት የነፃነት ታጋዮቹ አንዱአለም አራጌና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ አንድነት ፓርቲ የጀመረውን ህዝባዊ ንቅናቄ አበረታች መሆኑን አስምረው ሁሉም ኢትዮጵያዊ በንቅናቄው መሳተፍ እንዳለበት መክረዋል፡፡ ታጋዮቹ ለኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም ለጎንደርና ለደሴ መልዕክት እተላልፈዋል፡፡

ወጣቱ የነፃነት ታጋይ አንዱአለም አራጌ የኢትዮጵያ ህዝብ ለመብቱና ለነፃነቱ በሰላማዊ መንገድ መታገል አለበት ካለ በኋላ “በቅርቡ በአንድነት ፓርቲ በተጠሩት ሰላማዊ ሰልፎች ላይ የጎንደርና የደሴ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ ድምፁን ማሰማት አለበት፡፡ ሰላማዊ መሆናችንን ለሁሉም ወገን ማስመስከር ዘለብን” ብሏል፡፡

ታዋቂው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በበኩሉ ኢትዮጵያ ያለችበት ነባራዊ ሁኔታ ብሔራዊ ውርደታችንን የሚያሳይ መሆኑን አስረድቶ “የጎንደርና የደሴ ነዋሪዎች በህዝባዊ ንቅናቄው ተሳተፉ፣ ሰላማዊ ሰልፉ ላይ በንቃት ተሳተፉ ድምፃችሁን ፍፁም ሰላማዊ በሆነ መንገድ አሰሙ፡፡ ሳር እንኳን እንዳይበጠስ ጠጠር እንኳን እንይወረወር” ብሏል፡፡

‎#millionsofvoicesforfreedom ‎#Ethiopia ‎#UDJ

No comments:

Post a Comment