Sunday, July 21, 2013

የፓትርያርኩ ልዩ ጽሕፈት ቤት ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን ዘጋ

-    ‹‹ኮሌጁን የመዝጋት መብት ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ ነው››  የመንፈሳዊ ኮሌጁ ተማሪዎች

ከመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ተማሪዎቹ በሚያነሷቸው የተለያዩ ጥያቄዎች፣ የመማር ማስተማር ሒደት ሲስተጓጎል በመቆየቱና ባለፈው ሳምንት ደግሞ የሁለተኛ መንፈቅ ዓመት አጠቃላይ ፈተና እንዳይሰጥ ተስተጓጉሏል በሚል ምክንያት፣ የኢትዮጵያ ኦሮቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት፣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የቀን ተማሪዎች ትምህርት ተቋርጦ እንዲዘጋ አደረገ፡፡

በመንበር ፓትርያርኩ ልዩ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ብፁዕ ዶ/ር አቡነ ገሪማ ፊርማ የወጣው ደብዳቤ እንደሚያስረዳው፣ ኮሌጁ ከሐምሌ 8 ቀን 2005 ዓ.ም. እስከ መስከረም አጋማሽ 2006 ዓ.ም. ድረስ ተዘግቷል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሐምሌ 1 ቀን 2005 ዓ.ም. ሲሰጥ የነበረውን የሁለተኛ መንፈቅ ዓመት አጠቃላይ ፈተና ተማሪዎቹ እንዳይሰጥ በማድረጋቸው ነው፡፡ ተማሪዎቹ ፈተናው ይሰጣል በተባለበት ዕለት የኮሌጁን ቢሮዎች በመዝጋትና ሊፈተኑ የመጡ መምህራንን በመከልከላቸው መሆኑን ደብዳቤው ያስረዳል፡፡ እንዲዘጋ በጽሕፈት ቤቱ ውሳኔ የተላለፈበት የቀኑ የትምህርት ክፍለ ጊዜ ሲሆን፣ ተማሪዎቹም ለሐምሌ 9 ቀን 2005 ዓ.ም. በሰላማዊ መንገድ የኮሌጁን ግቢ ለቀው እንዲወጡ በጥብቅ ያሳስባል፡፡  


‹‹ኮሌጁን የመዝጋት መብት ያለው የከፈተው ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ ነው፤›› በማለት ተማሪዎቹ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጻፉትን ደብዳቤ በመቃወም ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ 

ተማሪዎቹ እንደገለጹት፣ ቀደም ብሎ በኮሌጁና በአስተዳዳሪዎች መካከል ተፈጥሮ በነበረው አለመግባባት ትምህርት መቋረጡ እውነት ነው፡፡ በመሆኑም የሁለተኛ መንፈቅ ዓመት የትምህርት ጊዜ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ ሊጠናቀቅ አልቻለም፡፡ ፈተና ይሰጣል የተባለበት ተመራቂ ተማሪዎች በመመረቂያ ጽሑፋቸው ላይ ‹‹ዲፌንስ›› የሚያደርጉበት ቀን በመሆኑ መጨናነቅ እንዳይፈጠርና የፈተና ጊዜያቸው እንዲራዘምላቸው የኮሌጁ የበላይ ኃላፊን አቡነ ጢሞቲዎስን ለማነጋገር ሐምሌ 1 ቀን 2005 ዓ.ም. በቢሯቸው መገኘታቸውን አስረድተዋል፡፡

ኃላፊውን ለማግኘት በቢሯቸው በራፍ ላይ በመጠባበቅ ላይ እንዳሉ ‹‹ችግር ሊፈጥሩብዎት እየጠበቁዎት ነው›› የሚል የተሳሳተ መረጃ ስለደረሳቸው አቡነ ጢሞቲዎስ ሳይገኙ በመቅረታቸው፣ ተማሪዎቹ ‹‹አንማርም፣ ፈተና አንፈተንም›› ብለዋል የሚል ክስ ወይም ከእውነት የራቀ አቤቱታ እንደቀረበባቸው ተማሪዎቹ ተናግረዋል፡፡

ልዩ ጽሕፈት ቤቱ የኮሌጁ ኃላፊዎችንና ተማሪዎችን ጠይቆ መረዳት ሲችል በሌለው ሥልጣን እንዲሁም ቀደም ብሎ በተማሪዎቹና በኮሌጁ ኃላፊዎች መካከል ተፈጥሮ በነበረው አለመግባባት ተማሪዎቹ ክስ ሲመሠርቱ፣ በክሱ ውስጥ ባካተቷቸው ብፁዕ አቡነ ገሪማ ፊርማ ኮሌጁ መዘጋቱ እንዳስገረማቸው ገልጸዋል፡፡ 

ተማሪዎቹ ለቅዱስ ሲኖዶስ በጻፉት ደብዳቤ የጠየቁት ኮሌጁ እንዲዘጋ የተጻፈው ደብዳቤ ሕጋዊ ባለመሆኑ በሕገ ቤተ ክርስቲያን እንዲታይላቸው፣ ቦርዱ እንዲያጣራ የተሰጠውን ኃላፊነት ለስድስት ወራት ዝም ብሎ ከርሞ ከተጠያቂነት ለመሸሽ በመሆኑ በሕግ እንዲታይላቸው፣ ቦርዱ የመንግሥትና የኮሌጁን ጊዜ በማጥፋቱ ዕርምጃ እንዲወሰድበት ነው፡፡ 

በኮሌጁ አስተዳደርና በተማሪዎቹ መካከል አለመግባባት መፈጠሩ ቢታወቅም ቅዱስ ፓትርያርኩን ሊያነጋግሯቸው እየለመኑ መሆኑን የሚገልጹት ተማሪዎቹ፣ ኮሌጁ እንዲዘጋ በብፁዕ አቡነ ገሪማ የተጻፈው ደብዳቤ ለቅዱስ ሲኖዶሱ ግልባጭ አለመደረጉ፣ ኮሌጁ የተከፈተው ለመደበኛ ተማሪዎች ሆኖ ሳለ ‹‹የንግድ ማዕከል አደረጉት›› በማለት በመጮኻቸው የቀን ተማሪዎች ብቻ እንዲባረሩ መደረጉ ተገቢና ቤተ ክርስቲያንም እንደማትፈቅድ ተናግረዋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም በቃለ በሕጉ መሠረት በምልዓተ ጉባዔው የአስቸኳይ ጊዜ ጥሪ አድርጎ እነሱንና ኮሌጁን ከአደጋ እንዲታደግላቸው ጠይቀዋል፡፡   

ምንጭ፡ ሪፓርተር ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment