Tuesday, July 2, 2013

ስፖርታዊ ግልሙትና

ስፖርት ታላላቅ የአካልና የመንፈስ እሴቶችን ለሰው ልጆች ካበረከተው በላይ ሕዝብን በማቀራረብ ወንድማማችነት እንዲሰፍን መራራቅን በማስወገድ አብሮነትን በማጠናከር ረገድ አቻ የማይገኝለት በዓለማችን ላይ መልካም ነገር ቢኖር ስፖርት ብቻ ነው። ስፖርት በተለይ ለኛ በስደት ላለነው ለኢትዮጽያዊያን ከደረሰብን የመለያየትና የመጠፋፋት ዘመቻ በማርገብ ረገድ ያስገኘልን ጥቅም ቃላት ሊገልጸው ከሚችለው በላይ ለመሆኑ የ30 አመታቱ የሰሜን አሜሪካው ስፖርት ማህበር ጉዞ ከአባት ወደ ልጅ ትውልዳዊ ሽግግር የደረሰበትን ታሪካዊ ጉዞ መጥቀሱ ብቻ በቂ ይመስለኛል። ከዚህም በላይ በሃገር ውስጥ ያለው ወገናችን በዘር ፖለቲካው የጎሪጥ እንዲተያይ ተደርጎ በተለያየ ጽንፍ ጠርዝ ይዞ በቆየበት ባለፉት ሃያሁለት አመታት ውስጥ በጋራ በአንድ ድምጽ የቆመበት አጋጣሚ ቢኖር የአትሌቶቻችን ስፖርታዊ ድልና የብሄራዊ ቡድናችን ከ30 አመት በኋላ የተቀዳጀው ውጤት ምን ያህል የሁላችንንም ስሜት ፈንቅሎ ከዳር እዳር እንዳስፈነጠዘን የነበረውን የጦዘ ልዩነትን በማለዘብ ትከሻ ለትከሻ አስተቃቅፎ እንዳቆመን በቅርቡ ያየነው ነው።

ይህን አቀራራቢ የአብሮነት መዐድ ለፖለቲካ መጠቀሚያነት ለማዋል በሃገር ውስጥ ያለው ዘረኛው የወያኔ አገዛዝ የብሄራዊ ቡድናችንን ውጤት ሳይቀር ለዛ ነብሰ ገዳይ መሪያቸው መለስ ዜናዊ መታሰቢያ ለማድረግ ያደረጉትን አሳፋሪ ተግባር ከያቅጣጫው በተነሳባቸው ተቃውሞ ቢተውትም ርካሽ አላማቸውን ለማሰራጨት የሚያደርጉትን ኢ-ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ካለማቆማቸውም በላይ ቀን ያነሳውን ተባባሪያቸው የሆነውን ከበርቴ ግለሰብ በሃገሪቱ ስፖርት ተቋማት ላይ እንደልቡ እንዲጋልብበት አጋር በመሆን እየፈጸሙ ያለውን አሳፋሪ ተግባር ወደ ባህር ማዶም በማሸጋገር ለሦስት አስዕርተ አመታት በስደተኛው ወገን ትጋትና ጥረት ጎልብቶና ዳብሮ ወደ ህዝባዊ ተቋምነት ያደገውን የስፖርት ማሕበር ለመንጠቅና የሰው በላውና ሃገር አፍራሹ የትግራይ ወያኔ ዘረኛና አሸባሪ ቡድን መጠቀሚያ ለማድረግ የተካሄደው ሴራ በሃገር ወዳድና ኩሩ በሆኑ የስፖርት ማህበሩ አመራሮች ተጋድሎ ህልውናውን ማስጠበቅ ቢቻልም ህሊናቸውን በሆዳቸው በለወጡ ጥቂት ክብረ ቢሶችን በመለቃቀም ተገንጣይ ቡድን በማቋቋም ህዝባችንን ለመከፋፈል የተካሄደው ዘመቻ የመጀመሪያው ምዕራፍ በሃፍረት እንደተጠናቀቀ የምናስታውሰው ሲሆን ለዳግም የግልሙትና ዘመቻም ሃይላቸውን አሰባስበው ከተራበው ህዝባችን በተነጠቀ የደም ገንዘብ መቃብሩ ላይ ጮቤ ሊረግጡ ሊገለሙቱና ሰይጣናዊ ሁከታቸውን ሊያካሂዱ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ዘንድሮም በመቀጠላቸው ሃገር ወዳዱ ወገን በማጋለጥና በመቃወም ታሪካዊ ሃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል።

ከሁሉ የሚያሳዘነው በዚህ በምዕራቡ ዓለም ያለ በሃገሩ መኖር አቅቶት ለስደት የበቃው ዲያስፖራ በጸሎት በተማጽኖና በብዙ ውጣ ውረድ የመኖር ነጻነቱ ተረጋግጦለት ሰብዓዊና ቁሳዊ ነጻነቱ ተረጋግጦለት ያለ ችግርና ችጋር ምቹ የሆነ ኑሮ ተቀዳጅቶ እያለ እንደ ምንዱባን ወገኑን ከሚያርዱት ሃገሩን ከሚሸጡት ዘራፊና ነብሰገዳይ ወንበዴዎች ጋር በመተባበር ከዛ የኑሮ ዳገት ከከበደው በልቶ ማደር ጣር ከሆነበት ፍትህና ነጻነት ተነፍጎ በስቃይ ከሚቃትተው ወገኑ በተነጠቀ ገንዘብ በመደለል ምንም ሳያጣ የከበርቴ ተንበርካኪና ክብሩን አሳልፎ የሰጠ ሎሌ በመሆን ወገንን የሚያሳዝን ታሪኩን ከሚያቆሽሽ መርገማዊ አድራጎት የተዘፈቁትን ጥቂት ሕሊና አልባ ግለሰቦች ያላወቁት የሕዝባችንን ተነሳሽነት ከቀድሞው በበለጠ እንዲጠናከር እልህ ውስጥ በመክተት አወንታዊ ሁኔታ ፈጠሩ እንጂ ፈጽሞ አንድነታችንን ሊያነቃንቁት አለመቻላቸውን ትላንት በቴክሳስ እንዳዩት ዛሬም በበለጠ በዲሲ ተደግሞ እንደሚያዩት አንጠራጠርም።

ስለዚህ ጥገኛ የአሽከሮች ስብስብ አንስቶ መነጋገሩ ኩሩ ለሆነው ለእኛ ለኢትዮጽያውያን የማይመጥን ቢሆንም ውሃን ድንጋይ ያናግረዋል እንዲሉ ይህው ተገንጣይ የከበርቴ ሎሌ የሆነ የፍንዳታ ጥርቃሞ ባለፈው አመት ከኢትዮጽያዊ ባህል ያፈነገጠ ርካሽና ዋልጌ አድራጎት ሲፈጸምበት እንደነበር የሂደቱን የተከታተሉ ወገኖች በቪድዮና በፎቶግራፍ በታገዘ መልኩ እንዳሳወቁን በነጻ ባቀረቡት የዳንኪራና የመጠጥ አቅርቦት ለአቅመ አዳም ያልደረሱ ለጋ ወጣቶች ሳይቀር በየጎዳናው ሰክረው ሲናውዙና በየጥጋጥጉ ሲዳሩ የነበረበትን ያስተዋለ ዜጋ ዘንድሮም በዛው የደም ገንዘብ ይህንንኑ ርካሽ አድራጎት የሚፈጽሙት በመሆኑ ታዳጊ ወጣቶችን ወደነዚህ አጥፊዎች እንዳይሄዱ ወላጆች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጭምር የሰማው ላልሰማው በማስገንዘብ ትውልዱን ከአልባሌ ድርጊት የመጠበቅ ሃለፊነትን ሊወጣ ይገባል።

ከቴድሮስ ሓይሌ

No comments:

Post a Comment