Sunday, July 14, 2013

ከአርባ ሺህ በላይ የሚቆጠር የጎንደር ሕዝብ ድምጹን አሰማ


የአንድነት ፓርቲ በጎንደር የጠራዉ ሰላማዊ ሰልፍ በተሳካ ሁኔታ በሰላም ተጠናቀቀ።  ከአርባ ሺህ በላይ የጎንደር ሕዝብ በወኔና በድፍረት የወጣ ሲሆን፣  በዜማ በቀራርቶ በፉጨት የግፍ አገዛዝ እንደመረረዉ በአደባባይ አሰምቷል።

የጎንደር ሰልፍን የያዙ ኦዲዮ፣ ቪዲዮች በስፋት ወደፊት የሚቀርቡ ሲሆን፣ ከቃሌ የመወያያ መድረክ የተገኘ በጎንደር የነበረዉን ሰልፍ የያዘ ኦዲዮ ከዚህ እንደሚከተለው አቅርበናል።

ሰልፉ ሊደረግ ታቅዶ የነበረው፣  ያለፈው ሳምንት፣ ሰኔ 30 ቀን እንደነበረ ይታወቃል። የክልሉ ባለስልጣናት «ሰልፉ ለአንድ ሳምንት ይራዘም» ብለው በጠየቁት መሰረት፣ ዛሬ ሐምሌ 7 ቀን እንዲደረግ ተወሰነ። ሰልፈኞቹ በየትኛው መንገድ ከየት ተነስተዉ፣ የት ሰልፋቸውን ማቆም እንዳለባቸው ፣ የዞኑ የፓርቲዉ አባላት፣ከባለስልጣናት ጋር ስምምነት አድርገዉ የነበረ ቢሆንም፣ የዜጎችን የመናገር መብትን፣ አይን ባወጣ መልኩ፣ ካድሬዎች ሲጋፉ በይፋ የታየበት ወቅት ነዉ።

ሰልፈኞቹ ብዙ ሕዝብ በሚገኝበት አካባቢ የሚወስዱ መንገዶች እንዲቀየሩ ሁለት ጊዜ ተደርጓል።  ወደ ዋናዉ ሰፈር ወደ ሚወስደው  መንገድ ሰልፈኞች፣  በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ፣ ለሶስተኛ ጊዜ መንገድ እንዲቀየሩ በሚጠየቁበት ጊዜ፣  «እምቢ አሻፈረን» በማለታቸው ከግማሽ ሰዓት በላይ ከፍተኛ ፍጥጫም ተከስቶም ነበር።፡

ካድሬዎች መፈክር የሚያሰማ የነበረዉን መኪና ከበዉ እንዳይንቀሳቀስ አድርገዉ የነበረ ቢሆንም፣  ሕዝቡ ግን ገፍቶ በመሄዱ፣ ካድሬዎቹ መኪናዉን ለመልቀቅና ሰልፉ እንዲቀጥል ለማድረግ ተገደዋል።

ምንጭ፡ ፍኖተ ነፃነት

No comments:

Post a Comment