Thursday, July 11, 2013

ዛሬ በደሴ ‹‹የሼኽ ነሩአዊ ሐረካት›› ድራማ ቀረጻ በመንግስት ተካሄደ

መንግስት የቱን ሕዝብ ነው ሊያታልል የሚሞክረው?

ከመንግስት ከፍተኛ የሚዲያ ዘመቻ ጀርባ ያለው ድብቅ አላማ ምንድን ነው?

ከሳምንት በፊት የተገደሉትና ምንም አይነት የአስከሬን ምርመራ (Autopsy) ሳደረግባቸው በችኮላ እንዲቀበሩ የተደረጉትን የሼኽ ኑሩን ግድያ መንግስት ባሰበው መልኩ ፖለቲካው ጥቅም ሊያፍስበት በመጣር ላይ ይገኛል፡፡ ይህን ለማሳካት እንዲቻለውም የተለመደውን ስልት በመጠቀም በደሴና አካባቢው በሚገኙ ከተሞች የግዳጅ ሰልፍ በማስወጣት በሚዲያዎች የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ ያደረገ ሲሆን፣ በመንግስት ብዙሀን መገናኛዎች በተለይም በኢቴቪና በአዲስ ዘመን ከፍተኛ የማራገብ ስራ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ መንግስት በተጨማሪም በሚኒስቴር መስሪያቤቶች እንዲሁም በፓርቲ ደረጃ ትናንት መግለጫ አውጥቷል፡፡ መንግስት በዚሁ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻው በመቀጠል ሼኽ ኑሩአዊ ሀረከት ድራማን በዜናና በሌላ የፕሮግራም ፎርማት ለማቅረብ የሚረዳውን ቀረጻ አካሄዷል፡፡ ይህ ድራማም ተቀናብሮ ዛሬ ምሽት ወይም ከሰሞኑ ለማታለያነት ለሕዝብ ይቀርባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ይኽው ዛሬ በደሴ ከተማ ሰኞ ገበያ ባድራ ጊቢ በተለምዶ አጠራሩ ረሺድ መስጊድ አካባቢ በመካሄድ ላይ የሚገኘው የድራማ ቀረጻ በከፍተኛ ጥንቃቄ በመካሄድ ላይ የሚገኝ ሲሆን የድራማው ግብአት እንዲሆኑ እየተደረጉ ያሉትም የደሴ ከተማ ወጣቶች ናቸው፡፡ እንደምንጮች ዘገባ ሼኽ ኑሩ ከመገደላቸው በፊትና ከተገደሉም በኋላ የተያዙ የከተማው ሙስሊሞችን የዚሁ ወንጀል ተጠያቂ ለማድረግ ዝግጅት ሲደረግ የቆየ ሲሆን በዛሬው እለትም ይህንን ውንጀላ በድራማ መልኩ ሲቀርጹ ውለዋል፡፡ ቀረጻው በሚካሄድበት ቦታ ዛሬ ከፍተኛ ጥበቃ ሲደረግ የቆየ ከመሆኑም በላይ በአካባቢውም ማንም ዝር እንዳይል ተደርጓል፡፡

የካሜራ እና ፊልም ባለሞያዎች ከመንግስት ከፍተኛ ደህንነቶች በተሠጣቸው ስክሪፕት መሰረት ሷሊህ ሙሀመድ የተባለና ማክሰኞ ከሰዓት አካባቢ ተይዞ የነበረን ወጣት ዛሬ በማለዳው ወደ መኖሪያ ቤቱ ይዞ በመሄድ ቀረጻ አካሄደዋል፡፡ ለቀረጻው ግብአት እንዲመችና ሕዝብንም መሸወድ እንዲቻል መንግስት በወጣቱ መኖሪያ ቤት ውስጥ የተለያዩ የጦር መሳሪያዎች እንዲቀመጡ በማድረግ ከወጣቱ መኖሪያ ቤት እንደተገኙ ተደርጎ ቀረጻ ተካሄዷል፡፡ በመቀጠልም ወጣቱ ሽጉጥ በእጁ እንዲይዝ በማስገደድ በቪዲዮ ቀርጻ የተካሄደበት ሲሆን፣ ሟችን ወጣቱ እንደገደላቸው አድርጎ ለማቅረብም ድራማው የሚያስፈልጉትን ዝግጅቶች መንግስት አከናውኗል፡፡ የወጣቱ ወላጅ እናትም የወንጀሉ ተባባሪ በሚል በእስር ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

የዛሬ የተካሄደውን የድራማ ቀረጻ ለማጀብ በርካታ የአካባቢው እና የክልል ባለስልጣናት እንደነበሩ የታወቀ ሲሆን የነበረው ጥበቃም ከፍተኛ ነበር፡፡ መንግስት የሼኽ ኑሩን ግድያ ተንተርሶ እያካሄደው ያለው ዘመቻ ቀድሞ ከፍተኛ ዝግጅት የተደረገበት መሆኑን ፍንጭ ሰጪ ከመሆኑም በላይ ጉዳዩን ሚዲያ ላይ ያራገበበት መንገድም አስገራሚ የሚባል ኖኗል፡፡ ላለፉት በርካታ አመታት በማህበረሰቡ ውስጥ አንቱታን ያተረፉ ከሌሎች እምነቶችም ሆነ ከሙስሊሙ ወገን አንጋፋ ሰዎች ህይወት ሲያልፍ ከመጤፍ ሳይቆጠር በሼኽ ኑሩ ሞት ተስታኮ ተከታታይ እና ከቀበሌ እስከ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የተቀናጀው ፕሮፖጋንዳ ከጀርባው ያለውን መልእክት በራሱ የሚናገር ነው፡፡ከጥቂት ሳምንታት በፊት ህይወታቸው ያለፈው ታላቁ አሊም ሀጂ ዘይኑ፣ ዶ/ር አብዱረሺድና ሌሎችም አሊሞች በመንግስት ሚዲያዎች ሞታቸውን አስመልክቶ ዘገባ እንዳልተሰራላቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ በባህር ዳር በቅርቡ ከ15 በላይ ንጹሀን ዜጎች በፌዴራል ፖሊስ ተገድለው ተገቢው የሚዲያ ሽፋን እንዳልተሰጣቸውም ይታወሳል፡፡

መንግስት ግን ይህን የሼኽ ኑሩን ግድያ በማጎን ሙስሊሙን ህብረተሰብም የወንጀሉ ፈጻሚ አድርጎ በማቅረብ ላይ ይገኛል፡፡ በክልል የሚካሄዱ የመብት ጥያቄዎችን ለማጨናገፍ የሰላማዊ ዜጎችን ንፁህ ደም በከንቱ ማፍሰሱ ሳይበቃ ድንበር ዘለል ፍረጃው እና ወከባው ከአሳሳ እስከ ደጋን፣ ከሃረር እስከ አዲስ አበባ የተተገበረ እና መላው ህዝባችንም የነገሩን ስር መሰረት በበቂ ማስረጃዎች ቀድሞውኑ ሲረዳው የነበረ ጉዳይ ነው፡፡ መንግስት ባወጣቸው መግለጫዎች ሙስሊሙን የወንጀሉ ፈጻሚ አድርጎ እያቀረበ ቢሆንም፤ ሙስሊሙ ህብረተሰብ መሰል ወንጀሎችን ለመፈጸም ሀይማኖቱም ሆነ መርሁ የማይፈቅድለት መሆኑና ሁለት አመት በዘለቀው ትግላችንም መሰል ወንጀል ተፈጽሞ አለማወቁ ምስክርነት ይሰጣል፡፡ የትግላችን መሰረታዊ መርህ የሆነው ‹‹የምንሞትለት እንጂ የምንገድልበት አላማ የለንም›› መርህ እንኳን በዚህ ወቅት አይደለም መሪዎቻችንን በተነጠቅንበትና ከፍተኛ ወንጀል በተፈጸመባቸው ወቅትም ተጥሶ የማያውቅ መሆኑን ሁሉም ህብረተሰብ የሚያውቀው የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡

የህዝባችን እና የትግላችን ሰላማዊነት የሚመነጨው ከምንከተለው መርህ መሆኑ ላለፉት 16 ወራት በተዘጋጁልን የትንኮሳ ወጥመዶች ውስጥ ላለመውደቅ ባደረግነው እልህ አስጨራሽ ትግል ፈተናዎችን በሚገባ በማለፍ አስመስክረናል፡፡ ሰላማዊው የደሴ ሙስሊምም እንደተቀሩት የሃገራችን ከተሞች በመቻቻል እና በመከባበር የሚኖር መሆኑ በአርዓያነት የሚነገር ነው፡፡ የደሴ ህዝብ እና መላው የሃገራችን ዜጎችም ከታሪካችን እና ከለመድነው ማህበራዊ መስተጋብር የወጣ ይህን መሰሉ ድርጊት ሲፈፀም አዳዲስ እጆች ሰርገው እንደገቡ ይረዳል፡፡ እነዚህ እጆች ደግሞ ሰላማዊ የመብት ጠያቂዎችን ለማፈን በተለያየ መጠን እና ግዜ ሲሰነዘሩ ሕዝቡ በበርካታ አጋጣሚዎች በአይኑ እየታዘበ በልቦናው አኑሯቸዋል፡፡ ሙስሊሙ ህብረተሰብ የዚህ አይነት ወንጀል የሚፈጽሙ አካሎች ቢኖሩ እንኳ ከማጋለጥ ወደ ኋላ እንደማይል የተረጋገጠና መሰል ወንጀሎችን እንደሚያወግዝ ደጋግሞ በአቋሙ አሳይቷል፡፡

አላሁ አክበር!

No comments:

Post a Comment