Thursday, July 4, 2013

ወያኔ እያለ ሙሰኝነትን ማጥፋትም መዋጋትም አይቻልም!

ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ ባለፉት ሃያ አንድ አመታት ማንነቱን ከገለጸበትና የዚህ ዘረኛ ስብስብ ተክለ ሰዉነት ቀዳሚ መገለጫ ከሆኑ ሁለት ትልልቅ ባህሪያት ዉስጥ አንዱ ሙሰኝነት ሲሆን ሌላዉ ዘረኝነት ነዉ። የወያኔ ስርአት የተገነባዉ በሙሰኝነት ላይ የቆመዉም ለሙሰኝነት ነዉ። ወያኔንና ዘረኝነትን ነጣጥሎ ማየት እንደማይቻል ሁሉ ወያኔንና ሙሰኝነትንም ነጣጥሎ መመልከት በፍጹም አይቻልም። ኢትዮጵያ ዉስጥ ወያኔና ስርአቱ በስልጣን ላይ እስካሉ ድረስ ሙሰኝነትም ይኖራል። ወያኔ ባለፉት ሦስት ወራት ይህንን የኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ ሳይሆን የአለም ህዝብ ጭምር በግልጽ የሚያዉቀዉን አስቀያሚ ገጽታዉን ለመሸፈን “ሙሰኝነትን አጠፋለሁ” በሚል ሽፋን አንዳንድ የሽንገላ እርምጃዎችን መዉሰድ ጀምሯል: አህያውን ፈርቶ ዳውላውን እንዲሉ:: በዚህም እርምጃው የሙሰኝነትን ምንጭና ባላባቶች ሳይሆን ስርአቱ በሙሉ ድምጽ የይሁንታ ምልክት ሳይሰጣቸዉ ሙሰኘነት ዉስጥ የተዘፈቁ ትናንሽ ሙሰኞችን በማሰርና ፍርድ ቤት በማቅረብ አንዳንድ ለአገራቸዉ በጎና ቀና አስተሳሰብ ያላቻዉን ዜጎች ለማታለል ይሞክራሉ።

የወየኔን ዘረኛ አምባገነን ስርዐት ከቀደሙት ስርአቶች ለየት የሚያደርገዉ ነገር ቢኖር ስርዐቱ ከፍተኛ የሃላፊነት ቦታ፤ የትምህርት እድል እንዲሁም የስራና በኢኮኖሚ የመበልጸግ እድል የሚሰጠዉ “ወርቃማዉ ዘር” እያለ ለሚጠራዉ የራሱ ወገን መሆኑ ብቻ ሳይሆን የአገሪቱን ያለ የለለ ጥሪት ያለገደብ እንዲቦጠቡጡ የሙሰኝነቱን በር ወለል አድርጎ የከፈተዉም ለዚሁ “ወርቃማዉ ዘር” እያለ ለሚጠራዉ ወገን መሆኑም ጭምር ነዉ። ይህም ኢትዮጵያ ዉስጥ ሙሰኝነት የተፈቀደላቸዉና ያልተፈቀደላቸዉ ዜጎችና ተቋሞች እንዳሉ በግልጽ ያሳያል። በቅርቡ በዜና ማሰራጫዎች ሙሰኝነታቸዉ ተጋልጦ ታሰሩ እየተባለ የተነገረላቸዉ ግለሰቦች ወያኔ ከፈቀደላቸዉ በላይ በሙሰኝነት የከበሩ ወይም ከከፍተኛዎቹ የወያኔ ሹሞች ጋር የስልጣን ሽሚያ ዉስጥ የገቡ ግለሰቦች ዳውላዎች ናቸዉ።

ባለፈዉ ሳምንት ማብቃያ ላይ ጠ/ሚኒስተር ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ለአገር ዉስጥ ጋዜጠኞች የሰጠዉ ጋዜጣዊ መግለጫ በግልጽ እንደሚያሳየዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ በሙሰኝነት ላይ እንዲሰማራ ብቻ ሳይሆን የሙሰኝነቱን ዘርፍ እንዲመራ በህግ ያልተጻፈ ሀላፊነት ከተሰጠዉ ተቋም አንዱ የአገር መከላከያ ሚኒስቴር ነዉ። ባለፈዉ ሚያዚያ ወር የፌዴራሉ ዋና ኢዲተር መስሪያ ቤት ለፓርላማዉ ባቀረበዉ ሪፖርት ባልተሟላ ሰነድ ወጪ ሆኗል ብሎ በሪፖርቱ ካሰፈረዉ አምስት ቢሊዮን ብር ዉስጥ ሦስት ነጥብ ሁለት ቢሊዮኑ የመከላከያ ሚኒስትር መሆኑ የሚታወስ ነዉ። እዚህ ላይ አንድ የሚገርመን ነገር ቢኖር በቅርቡ ጠ/ሚኒስተር ኃ/ማሪያም ደሳለኝና የመከላከያ ሚኒስትሩ ሲራጅ ፈርጌሳ አንደተናገሩት ከሆነ የኢትዮጵያ ፓርላማ “ሚስጥር ለመጠበቅ” በሚል ሽፋን በሙሰኝነት እንዳይጠየቅ ህግዊ ሽፋን የሚሰጥ አዋጅ በማርቀቅ ላይ የሚገኘዉ ይህንኑ በሙሰኝነት የተዘፈቀዉን የመከላከያ ሚኒስትርን ሆድ ለመደበቅ ነዉ።


ለመሆኑ ሀላፊነቱና የስራ ድርሻዉ አገርን ከዉጭ ጠላት መጠበቅ የሆነዉ የወያኔ መከላከያ ተቋም በንግድ፤ በእርሻ፤ በኮንስትራክሺንና በከባድ እንዱስትሪ ግንባታ የስራ መስኮች ዉስጥ ያለቦታዉ ተዘፍቆ እየታየ ለምን ይሆን የዚህ ተቋም የሂሳብ መዝገብ በኦዲትሮች እንዳይታይ የሚደነግግ አዋጅ እንዲወጣ ያስፈለገዉ? ለምንድነዉ ጠ/ሚኒስትር ተብዬዉ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ የመከላከያና የደህንነት ተቋማት በኦዲተር አይመረመሩም ያሉት?

መልሱ ቀላልና ግልጽ ነዉ። ወያኔ የኢትዮጵያን ህዝብ ለማዘናጋት ሙስናን አጠፋለሁ ብሎ የጀመረዉ የዉሸት ዘመቻ ያነጣጠረዉ የአገሪቱን የመከላከያ ተቋም ሙሉ በሙሉ በሚቆጣጠሩት የወያኔ ጄኔራሎች ላይ በመሆኑ ነዉ። ወያኔ የሾማቸዉ የራሱ ኦዲተሮች አመታዊ የሂሳብ ቁጥጥር ሪፖርት በግልጽ እንደሚያመለክተዉ ከፍተኛ የሂሳብ ጉድለትና የመዝገብ አያያዝ ዝርክርከነት የታየባቸዉ ወያኔያዊ ተቋሞች የመከላከያ ሚኒስቴር፤ ብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎትና የአገር ዉስጥ ደሀንነት ጥበቃ ዋና መምሪያ ናቸዉ። ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ከህወሃት አለቆቹ በተሰጠዉ ቀጭን ትዕዛዝ መሠረት ወንጀላቸዉን ለመደበቅ ህጋዊ ድጋፋ እንዲያገኙ የሚጣጣረዉም ለእነዚሁ ሦስት ተቋሞች ነዉ። እነዚህ ህዝብን ሰላም የነሱ፤ የአገሪቱን ሀብት ሙልጭ አድርገዉ የዘረፉና ተጠያቂነት የሚባል ነገር የማያዉቁ ስግብግበች የሞሉበትን ተቋም ጭራሽ ህግ ሽፋን ከተጠያቂነት ዉጭ ማድረግ የበለጠ እንዲዘርፉና በህዝብ ደም እንዲነግዱ ህገ መሰነግስታዊ እዉቅና መስጥት ነዉ።

ወያኔ ያሻዉን ያክል አስቀያሚ ገጽታዉን ሸፍኖ ለህዝብና ለአገር የሚያስብ መስሎ ለመታየት ቢሞክርም የኢትዮጵያ ህዝብ ግን እንኳን ሙሰኝነትን የመሰለ በአይን የሚታይ ጉልህ የወያኔ መታወቂያ ቀርቶ ወያኔ ለወደፊት ለማድረግ በዕቅድ የያዘዉን ሁሉ ከወዲሁ የሚያዉቅ ህዝብ ስለሆነ ሙሰኝነትንና በስልጣን መባለግን ለማጥፋት የመጀመሪያዉ ትግል ከወያኔ ዘረኞች ጋር መሆኑን ተረድቶ ትግሉን ቀጥሏል። ይህ የተጀመረ ህዝባዊ ትግል ወያኔንና ሁለቱን መንታ ልጆቹን ማለትም ሙሰኝነትና ዘረኝነት ከአገራችን ምድር እስኪነቀሉ ድረስ ይቀጥላል።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

No comments:

Post a Comment