Wednesday, July 3, 2013

ሞርሲ ተነሱ፣ ሕገመንግሥቱ ተቋረጠ

ሕገመንግሥቱን ማቋረጣቸውንና ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ሞርሲን ከሥልጣናቸው ማስወገዳቸውን የግብፅ ወታደራዊ አዛዥ አስታወቁ፡፡

የሃገሪቱ የጦር ኃይሎች አዛዥ ጄነራል አብዱል ፋታህ ኻሊል አል-ሲሲ ከተቃዋሚዎች ተወካዮች እና ከሐይማኖት መሪዎች ጋር ሆነው በሰጡት መግለጫ ሕገመንግሥቱን በጊዜያዊነት ማቋረጣቸውን ተናግረዋል፡፡

ተከታዩ መንግሥት በምርጫ እስኪሰየም ድረስም የሕገመንግሥታዊው ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ የሃገሪቱን የመንግሥት ሥራ አስፈፃሚ ሥራዎች እንደሚያከናውኑ አስታውቀዋል፡፡

የሽግግሩ ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ በወታደራዊው ዕቅድ የተሰየሙት የሕገ መንግሥታዊው ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ አድሊ ማሱር ባሰሙት ንግግር ደም መፋሰስን ለማስወገድ እንደሚጥሩ አስታውቀዋል፡፡ የአሁንን እርምጃ ያመጣው “ያለፈው መንግሥት” ለዕርቅ መሥራት ስለተሣነው መሆኑን የጠቆሙት አዲሱ ፕሬዚዳንት እርሣቸው ለዕርቅ እንደሚጥሩ ቃል ገብተዋል፡፡

የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎችና ወጣቶች በፖለቲካው ሂደት ውስጥ እንዲሣተፉ እንደሚያበረታቱ አዛዡ አስታውቀዋል፡፡

በጣሕሪር አደባባይ የተሰበሰቡ ተቃዋሚዎች ደስታቸውን በከፍተኛ ድምፅ እና ርችት እየተኮሱ እየገለፁ ሲሆን የሙስሊም ወንድማማችነት መሪዎች ቀደም ሲል በሰጡት መግለጫ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደ ነፃ ምርጫ የተመረጡ ፕሬዚዳንታቸውን ለመጠበቅ እንደሚፋለሙ ሲዝቱ እንደነበር ይታወቃል፡፡

ሚስተር ሞርሲ ያሉበት ቦታ ለጊዜው አይታወቅ እንጂ የፕሬዚዳንቱ ፅሕፈት ቤት በትዊተር ገፁ ላይ ባወጣው መልዕክት “ስለ ግብፅ እና ለታሪክም ትክክለኛነት ስንል እየተካሄደ ያለውን በስሙ እንጥራውና ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ነው” ብሎታል፡፡

የአል አዝሃር መስጂድ ዋና ኢማም ሼኽ አሕመድ አል ጠይብና የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ሊቀ-ጳጳስ አቡነ ቴዎድሮስ ዳግማዊ በየተራ ባደረጉት ንግግር አምላክ ግብፅንና ሕዝቧን እንዲጠብቅ ለምነዋል፡፡

የተቃዋሚዎቹ ተጠሪ ሞሐመድ አል ባራዳይ ባሰሙት ንግግር የጦር ኃይሎቹ ያቀረቡት ዕቅድ “የግብፅ አብዮት ባለፈው ዓመት የተነሣሣለትን ማኅበራዊ ፍትሕ እና ነፃነት ለማስገኘት የመንደርደሪያ ደንጊያ ነው” ብለውታል፡፡ አልባራዳይ አክለውም ይህ ዕቅድ “የአብዮቱ መንገድ ማስተካከያ እርምጃ ነው”ም ሲሉ ጠርተውታል፡፡

ዕቅዱ ከሚያካትታቸው ቁልፍ ካሏቸው ተግባራት መካከልም “ፈጥኖ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ማካሄድ፣ ሕገመንግሥታዊ ማሻሻያ ማድረግ፣ በሚሰየም የዕርቅ ኮሚሽን ብሔራዊ ዕርቅ መፍጠር” እንደሚገኙበት ዘርዝረዋል፡፡

የታማሮድ ወጣቶች  መሪ ባሰማው ንግግር እርምጃው በግብፅ ታሪክ ውስጥ አዲስ እርምጃ መሆኑን ጠቁሞ “ግብፅ መገፋት የሌለባት፣ ለክብራቸው፣ ለነፃነትና ለማኅበራዊ ፍትሕ እምቢ ባይ የሆኑት የሁሉም ግብፃዊያን የሆነች ሃገር ነች” ብሏል፡፡

በጊዛው ካይሮ ዩኒቨርሰቲ ትናንት በተካሄዱ ግጭቶች የ18 ሰው ሕይወት መጥፋቱ ተገልጿል፡፡

ጄነራል ሲሲ የሃገሪቱን መፃዒ ዕጣ ፈንታ ዕቅድ ያሉትን ካነበቡና የፕሬዚዳንቱን መወገድ ካስታወቁ ወዲህ የተፈጠረ ግጭት ይኑር ወይም አይኑር ለጊዜው በግልፅ የወጣ ዘገባ የለም፡፡

ምንጭ፡ ቪኦኤ 

No comments:

Post a Comment