Saturday, May 3, 2014

ኢትዮጵያ በህግ አምላክ የሚባልባት ሀገር መሆኗ ቀርቷል

ግፈኛውና ዘራፊው የወያኔ መንግስት በኢትዮጵያ መሬት ከሚሰራቸው ትልልቅ ወንጀሎች አንዱና ምናልባትም ዋነኛው በህግና ሕገ-መንግስት ላይ የሚያካሄደው ቀልድና ጭዋታ ነው። ሕገ-መንግስት ህዝብን ከእብሪተኛ መንግስት መጠበቂያ መሳሪያ መሆኑ ቀርቷል። ህግና ሕገ-መንግስት ለወያኔ ሲፋጅ በማንኪያ ሲበርድ በጣት የሚበላ ነገር ነው። ወያኔና አፋኝ ስርአቱ ህግ የሚጠቅሱት ለራሳቸው ይጠቅመናል ባሉበት ሰዓት ነው። ህግ ለነሱ ካልተመቻቸው ተቀዶ የሚጣል ቆሻሻ ወረቀት ነው።

በኢትዮጵያ ምድር ዋናው ሕገወጥ ተቋም ራሱ ላወጣው ሕግ የማይገዛው ወያኔ/ህወሃት ነው። ለዚህ ነው “ለሚመለከተው አካል ከማሳወቅ ውጪ ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ ፈቃድ አይጠየቅም” የሚለውን ራሱ ያወጣውን ህግ ጥሶ ሰሞኑን ተቃዋሚዎችን ቁም ስቅላቸውን የሚያሳያቸው። ለዚህም ነው ሃሳብን በጽሁፍና በቃል ለመግለጽ ቅድመ ምርመራ እና እገዳ አይኖርም ብሎ ጽፎ፣ አለም አቀፍ የሰበአዊ መብት ድንጋጌዎች እንዳሉ ተቀብያለሁ ብሎ የተናገሩና የጻፉ ሰዎችን የሚያሳድደውና በሽብርተኝነት የሚከሰው።

ኢትዮጵያ “በሕግ አምላክ” የሚባልባት ሀገር መሆኗ ቀርቷል። ወያኔ ይህን ለህግ ትልቅ ክብር ያለውን የህዝባችንን የዘመናት እምነት ድራሹን በማጥፋት ላይ ይገኛል። ፍትህ በወያኔ አፋኞች መዳፍ እጅ ወድቃለች።

በዚያ አስከፊ የደርግ መንግስት ስርአት እንኳን ዳኞችን “እንዲህ ብላችሁ ፍረዱ” የሚል ትእዛዝ አልነበረም።


ዛሬ በየፍርድ ቤቱ አለም እየታዘበ የሚከናወን አይን አውጣ አሰራር እና የህወሃት የንጹሃን ዜጎችን የፖለቲካ መቀጣጫ ቤት ሆኖ ተለምዶል። ፍትህ እና ፍርድ ቤት እንዲዋረድ ሆኗል። ፍትህና ዳኝነት ራሱ በህወሃት የታሰረበት ጊዜ ነው።

ባለፈው ሳምንት ወያኔ አፍሶ ማእከላዊ በማስገባት የሚያሰቃያቸው የዞን 9 የኢንተርኔት ፌስቡክ ተጠቃሚዎች በሀገሪቱ ህገ መንግስት ከተለመደው መሰረታዊ መብታቸው ውጪ ያደረጉት ቅንጣት ወንጀል የለም። ወያኔ በፈራ እና በደነገጠ ቁጥር ሺህ ህግ ይጥሳል፡፡ ወያኔ ደግሞ ጥላውን የሚፈራ ድንጉጥ ተቋም ነው።

የኢትዮጵያን ህዝብ እንደ ጠላት እንጂ እንደ አብሮ ኗሪ ዜጋ ማየቱን ከተዎ የሰነበተውም ለዚህ ነው።

ዛሬ ራሱ ወያኔም እኛም በሕግና በሕጋዊነት ላይ ያለን ተስፋ ተሟጧል። ስለዚህም ነው ምርጫችን ይህን ህገ ወጥ የወንበዴ መንግስት በትጥቅ አልባም ይሁን በታጠቀ ሁለገብ አመጽ ማስወገድ ብቻ ነው የምንለው።

ግንቦት 7 የወያኔን አያያዝ አይተን የሁሉአቀፍ የአመጹን መንገድ ተከትለናል። ፈልገን ሳይሆን ተገደን በወያኔ ምርጫ የተመረጠልንን።

የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ ወያኔ የህግና የሰላም በሩን ሁሉ ዘግቶ የተወልህን እና ሊከለክልህ የማይችለው ምርጫ የራስህን የነጻነት ትግል የአመጽ ሃይል ብቻ ነው። በየአለህበት በእምቢተኝነት ተነሳ!! መብትህንና ክብርህን ከወያኔ መጠበቅ የዋህነት ነውና ተነስ ተቀላቀል! ራስህን ነጻ አውጣ።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

No comments:

Post a Comment