Thursday, October 10, 2013

በሃገራችን የአባታዊነት ወረርሽኝ በሽታ ይወገድ (ከአስገደ ገ/ስላሴ ከመቐለ)

አባታዊነትና ሎሌነት ለአገር እድገት እንቅፋት ናቸዉ።

ኢትዮጵያ አገራችን ቀደም ሲል የንጉሱ የዘውድ አገዛዝ እኔን ያላከበረ ያላመለከ እኛ ያልነዉ ያልታዘዘ በዚች ምድር አይኖራትም ይሉን ነበር።ከአባታዊነትም አልፎ ለንጉሱ የአምላክን ያህል እንዲያመልክ ይታዘዝ ነበር።የዘውዳዊ ስርአት ግን የተሻለ ነበር።

ኃላም የዘውዳዊ አባታዊ ስርአት በጭቁኖች ተቃውሞና ትግል ተፍረክርኮ ሲወድቅ በወቅቱ ይደረግ የነበረ ትግል ያልተደራጀና ሲቪላዊ የሆነ የተረዳጀ ፓርቲ ስላልነበረ የአባታዊ ዘውዳዊ ስርአት አገልጋይ የነበረ ወታደራዊ ደርግ በትረ ስልጣን ጨብጦ ከአባታዊነት በባሰ አንባገነናዊና ገዳይ ወታደራዊ ደርግ ተተካ።

§     ደርግ ገና አንድ አመት ሳይቆይ በወቅቱ 60ሚሊዮን አካባቢ ለነበረዉ ህዝባችን በመዳፉ ስር በማስገባት ሁሉንም አይነት ነፃነት በማፈን የመናገር፣ ሃሳብን በነፃ የመግለፅ ፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ፍፁም አባታዊ በሆነ መንገድ በአዋጅ ዘጋዉ መላዉ ህዝባችን መፈናፈኛ አጥቶ ግማሹ ነፍጥ አንስቶ ወደ ትግል ሜዳ ሲወርደ ሌላዉ ለስደት ተዳረገ፣፣ የቀረዉ ህዝብ ለ17 አመት በአባታዊ ፋሽስት ደርግ ታፍኖ ኖረ።

§   በዛን ጊዜ የዘውዳዊ አገዛዝና የደርግ ፋሽስታዊ ስርአት አገዛዝ በመቃወም ደርግ ለመጣል በሰላማዊ መንገድ አይቻልም ብለዉ በወቅቱ የነበሩ ምሁራኖች ለወዛደሮች ጭቁን ገበሬዎች በማንቃትና በማደራጀት እንዲሁም ባልተደራጀ በተናጠል በሁሉም የሃገራችን ክልሎች ብሄር ብሄረሰቦች ተሰማርተዉ በፖለቲካ ፓርቲና በቡድን በመደራጀት አባታዊ ፋሽስታዊ ደርግን በትግል  ለመጣል ነፍጥ ይዘዉ ዘመቱ።

§  ወደ ትጥቅ ትግል የዘመቱ ወገኖችም ብዙም ጥናት ሳያደርጉ  በግብታዊነት አንዳንዶቹ የብሄር ጥያቄ ሌሎችም ምንም ታሪካዊ መነሻ የሌላቸዉ ከአማራ ቅኝ አገዛዝ ነፃ ለመውጣት ለመገንጠል የሚል አስተሳሰብ በመያዝ በሌላ አቅጣጫ የአንድነት ጥያቄ ግምት ላይ ያላስገባ አቋም የያዙም ነበሩ።መስመር በመያዝ ነገር ግን የነበረዉ የብሄሮች ግጭትና መቃቃር  ግምት ውስት ሳያስገቡ የተነሱ ነበሩ፣፣

§  በሌላ በኩል ደግሞ አንዳንድ ወገኖች በሃገራችን የሚደረግ ትግል በደርግ ስርአት ውስጥ ሆነህ አስተካክሎ በማረም ለውጥ ሊመጣ ይችላል ብለዉ ደርግ ከደርግ ጋር ሆነዉ ብዙ ድርጊት የተፈፀሙ ነበሩ።

§  ከላይ የተጠቀሱት ሃይሎች እምቢ ለፋሽስታዊ አባታዊ አገዛዝ ብለዉ በወኔ ለመታገል በመዝመት እጅጉን የሚያስመሰግናቸዉ ቢሆንም በየአቅጣጫዉ ወደ ትግል የዘመቱ ሃይሎች ተስማምተዉ በሚያገናኛቸዉ ሃሳብ  ካለ በውይይት ልዩነት በማጥበብ አብረዉ ለአንድ ጠላት እንደማጥቃት ፋንታ ከዘውዳዊ አገዛዝና ከፋሽስታዊ ደርግ በወረሱት የአባታዊነት ከኔ በላይ ላሳር በሚል ፈሊጥ የኔ መስመር (አላማ) ይበልጣል ከሚል አባታዊ የሆነ ትእቢት እርሰ በራሳቸዉ በነፍጥና በሌላ ውስጥ ለውስጥ ሴራ ተጫርሷል።

§  በዚህ የአባታዊነት ባህሪያቸዉና ስራቸዉ ዋናዎቹ ተጠቃሾች በወቅቱ የነበሩት ፓርቲዎች በሙሉ ተጠያቂዎች ቢሆኑም የሁሉም ባህሪያት በዚች አጭር ፅሁፌ የሁሉም ገመና ለማስቀመጥ ስለማይቻል  ህ.ዋ.ሓ.ት ከተፈጠረበት ዓ/ም እስከ አለንበት ዘመን አባታዊነት ተጠናውቶት የቆየውና ያለዉ ህ.ወ.ሓ.ት አመራር ቀደም ሲል በ17 አመቱ የትጥቅ ትግል ወቅት ረጂም ሳይጓዝ በጊዜዉ ከነበሩት ፀረ ደርግ ሃይሎች በነፍጥ የሚዋጉ ተስማምቶና ተቻችሎ ለአንድ ጠላት ተባብሮ ከመምታት ፈንታ ገና በጥዋቱ በሰሜን ኢትዮጵያ ለነበሩ ፖለቲካ ፓርቲዎች ከአያቱ ጃንሆይና ከአባቱ ደርግ የወረሰዉ  የአባታዊነት ባህሪ ህዝቦች ባሉበት አካባቢ ማንም ፓርቲ መንቀሳቀስ የለበትም በሚል በግንባር ገድሊ ሓርነት ትግራይ (T..L.F)   ( ግገሓት ) በመጨፍለቅ የጀመረዉ ኃላም ለተጋድሎ ሓርነት ትግራይ ጠርናፊት ኮሚቴ፣ ለኢድዩ፣ ለኢህአፓ በየተራ አጠፋቸዉ።

§  በህ.ወ.ሓ.ት ፓርቲ ውስጥ በአባላቱ ለሚነሱት ሃገራዊና አህጉራዊ ጥያቄ ስለዲሞክራሲና ስለሰብኣዊ መብት ጥያቄዎች ሲነሱ ሰከን ብሎ አስቦ በዲሞክራሲያዊ መንገድ አሳርጎ ከመፍታት ፈንታ በማሰር በመቅጣት በማባረር ነበር የሚፈታዉ። በተጨማሪ በፓርቲዉ ስለፖለቲካዊ ዲፕሎማሲያዊ  ፋይናንሳዊ ጥያቄ በሚነሳበት ግልፅነትና ተጠያቂነት ባለበት ፍትሃዊ መልስ እንደመስጠት  ፋንታ ለዚሁም ከኔ በላይ ላሳር በሚል አባታዊ  ፈሊጥ ነበር የሚያስተናግደዉ።

§  በአሁኑ ጊዜም ህ.ወ.ሓ.ት  ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ ከጥንት ጀምሮ  የነበረዉ የአባታዊነት ባህሪ ሳይከለስ በሃገራችን ህገ-መንግስት መሰረት አድርገዉ በተቃዋሚ ፖለቲካዊ ፓርቲ ተደራጅተዉ በሰላማዊ መንገድ ለሚታገሉ በትጥቅ ትግል ጊዜ እንደለመደዉ ህግ-መንግስትን በመጣስ እኔ ካልኳችሁ ግቡ ፤ውጡ በማለት አባታዊ ተግባራቱ በመፈፀም የሰላማዊ ትግሉን እያጨለመዉ ይገኛል።

§  በሌላ በኩል የህ.ወ.ሓ.ት መንግስት አባታዊ ባህሪውን በሰላማዊ  መንገድ ለሚታገሉ ፓርቲዎች  ብቻ አይደሉም  እየፈፀመ ያለዉ። መላዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ምሁሩ፣ ነጋዴዉ፣ ተማሪዉ፣ አርሶአደሩ፣ አርብቶቸደሩ፣ የመንግስት ሰራተኛ እኛ ባልንህ መንገድ ሂድ በማለት እንዳይናገር፣ እንዳይቃወም በስለላ  ወጥመድ በመያዝ እንዲሁም ትናንት መሬት የህዝብ  ነዉ ይል የነበረዉ አባታዊ ፓርቲ የገጠርም የከተማም መሬት የኔ ነዉ ብሎ ህዝቡ ዜግነቱ አጥቶ ሞራሉ እንዲነጠቅ አድርጓል።


§  የህዝቡ የምሁራኑ፣ የተማራማሪዎች የፖለቲካ ፓርቲ ተሳትፎ በማፈን በሃገራችን የልማት ሰራዊት በሚል ስም ( መፈክር) የቀበሌ ተላላኪዎች  ምንም ሞያ የሌላቸዉ ያገራችን ሃብት ለሙስናና ለጥፋት በመዳረግ የልማት እድገት እያጨለመዉ ይገኛል። የአባታዊነት ውጤትም ይህ ነዉ። በሃገራችን በሰላማዊ መንገድ  እንታገላለን የሚሉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከአባታዊነት ነፃ ናቸዉ ወይ?

§  ከ 39 አመት ወደ ኃላ  በመመለስ የህ.ወ.ሓ.ት ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ ፓርቲ የአባታዊነት ለመግለፅ የተገደድኩት ያላንዳች ምክንያት አይደለም ።

§  በሃገራችን ከ 22 አመት በላይ የህብረ ብሄር በብሄር ብሄረሰብ በሰላማዊ ፖለቲካ ፓርቲ ተደራጅተዉ ለ 4 ጊዜ ሃገራዊ ምርጫ ተሳትፈዉ አብዛኛዉ ምርጫ ታፍኗል፣፣ ሌላዉ ደግሞ  በፓርቲዎች ስህተት ተበላሽቷል።

§  የነዚህ ፓርቲዎች ዋንኛዉ ውድቀት

1ኛ ከህ.ዋ.ሓ.ት የወረሱት የአባታዊነት ወረርሽኝ የፈጠረዉ ውድቀት ነዉ። ምክንያቱም እነዚህ ፓርቲዎች ከላይ ተንሳፍፈዉ በውጭ ብዙሃን መገናኛ አለፍ አለፍ ብለዉም ባገር ውስጥ የግል ጋዜጦች   መግለጫ ከመስጠት አልፈዉ ለውጥ ሊያመጡ አልቻሉም።

2ኛ እነዚህ ፓርቲዎች ከ1983 ዓ.ም ጀምረዉ የተፈጠሩ ፓርቲዎች መሪዎቻቸዉ ህ.ወ.ሓ.ት መንግስታዊ ስልጣን ሲይዝ የያዙ ናቸዉ።

3ኛ እነዚህ ፓርቲዎች በአመራሩ ብቁ ምሁራን ከሁሉም የህብረተሰቡ ብቁ ዜጎች  ወደ ፊት አላመጡም

4ኛ በአዲስ አባ እና አልፎ አልፎም በጥቂት ክልሎች ትናንሽ ስብሰባ ከማድረግ ውጭ ወደ ዞን፣ ወረዳ፣ ቀበሌ ወርደዉ የህዝብ ማእበል አልፈጠሩም።

5ኛ የሚሰጡት መግለጫ በሃገር ውስጥ ይሁን በውጭ የወጣት ብቁ ምሁራኖች አያሳትፍም፣፣ በመሆኑ ባለፉት 22 አመታት የኢትዮጵያ ህዝብ በተቃውሞ አዳዲስ መሪዎችም አልመጡም ፣፣ ልክ እንደ ህ.ወ.ሓ.ት መሪዎች አባታዊነት  የተጠናወታቸዉ ናቸዉ ። ስለሆነም በፖለቲካ ፓርቲዎችም በአባታዊነት ምክንያት የተበላሸ ነገር አለ። በዚህ ላይ የአንድነት ፓርቲ የተሻለ ነገር እየሰራ ይመስላል ፣፣ ግን ደግሞ በተናጠል አያዋጣውም።

6ኛ በፖለቲካ  ኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ስራዎች አዲሱን ትውልድ አያሳትፉም፣፣ ሁሉም ነገር በነባር ፖለቲከኞች ነዉ የሚወሰነዉ፣፣ የሚሰሩት ሁሉ ግልፅነትና ተጠያቂነት የለዉም፣፣ ወጣቱ ትውልድ  ባገር ውስጥም ይሁን በውጭ ተንቀሳቃሽ የትግል ማእበል እንዳይፈጥር አፍነዉና አግተዉ  ይዘዉታል። ይህ አሰራር የህ.ወ.ሓ.ት ፎቶ ኮፒ ነዉ። በውጭም ይሁን በአገር ውስጥ ያላችሁ የተቃውሞ ፓርቲ መሪዎች ወጣቱ ፊት ሆኖ አገር እንዲመራ እንደማድረግ ፋንታ የህ.ወ.ሓ.ት የአባታዊነት ውርሻ (ሊጋሲ) በማስከተል በአባታዊነት (በትእቢት በመወጠር) ለሃገሪቱ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊ ዲሞክራሲያዊና ነፃነት በማሰብ ፋንታ የራሳቸውን ስልጣን የቆዳ ክብር በመጠበቅ አዲሱ ትውልድ  ነፃ ሆኖ እንዳይንቀሳቀስ ሁሉም ነገር ራሳቸዉ ብቻ ግልፅነት በጎደለው መፈፀሙ ስህተት ነዉ።

§  ይህ ተግባር በአሁኑ ጊዜ ይታይ ያለዉ የተቃውሞ ፓርቲ የህ.ዋ.ሓ.ት መሪዎች የአባታዊነት የወረርሽኝ በሽታ በመቅሰም ያለ አንዳች መሰረታዊ ልዩነት በውሃ ቀጠነ ልዩነት በመያዝ የሃገራችን መሰረታዊ ችግር እንደመፍታት ፋንታ ለየግላቸዉ በስልጣን ወጥተዉ ልታይ በማለት ላይ ተንሳፍፈዉ የተቃውሞ ሃይሉን እያመሱት ይግኛሉ። መሪዎች የ ህ.ወ.ሓ.ት ከፋንታ ለየግላቸዉ ስልጣን ልታይ ልታይ የተቃውሞ   ሃይሉን እያመሱት ይኖራሉ። ወጣቱ አዲሱ ትውልድ ምሁሩ፣ ባለ ሃብቱ፣ አርሶአደሩ ጭቁን የመንግስት ሰራተኛዉ ከህ.ወ.ሓ.ት መንግስት አፈና ለመላቀቅ አማራጭ አጥቶ ከሚጠላቸዉ የህ.ወ.ሓ.ት ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ መሪዎች ተለጥፎና ተንበርክኮ፣ ተሸማቅቆ እንዲኖር አድርገውታል።

§  ይህ ስለአዲሱ ትውልድ መላዉ ህብረተሰብ ለህ.ወ.ሓ.ት መሪዎች ይሁን በአሁኑ ጊዜ ያሉ የተቃውሞ መሪዎች  ይሁን አባቲዊነት መንበርከኩ ደግፈዉ አይደለም ይህ ትውልድ  እኔ የምመክረዉ በአሁኑ ጊዜ አባታዊነትና ከኔ በላይ ማን አባቱ የሚል ቦታ የለዉም 21ኛ ክፍለ ዘመን ነዉ። በሃገራችን ያለ ሁሉም አይነት አባታዊነትና ትእቢተኛነት የራሱ የተደራጀ ሃይል አዘጋጅቶ ማእበል በመፍጠር ጥሩ መሪዎች በመለየት ወደ ፊት መገስገስ  አለበት አባታዊነትን ተሸክሞ ለህ.ወ.ሓ.ት ወደ ወንበር የሰቀለ የትግራይ ህዝብም አልጠቀመዉም አባታዊነት ለመላዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ወደ ወጥመድ አስገብቶታል።

§  የአባታዊነት ባህሪ በህ.ወ.ሓ.ት መሪዎችና 22 አመት በተቃውሞ ጎራ የቆዩ ፖለቲካ ፓርቲ ብቻ አይደለም የሚታየዉ ወረርሽኑ በትግራይ ውስጥ ከተመሰረተ አሁን 5 አመቱ እያስቆጠረ ያለዉ በዓረና ትግራይም ገና ረጅም ሳንጓዝ የአባታዊነት ፈረስ በፍጥነት በመጋለብ በሃገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚደረገዉ የፖለቲካ የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዉ በፓርቲዉ ውስጥ ያሉ ብቁ ወጣቶች እንዳይሳተፉ ማድረግ ግልፅነት የማጉደል ለአባላት የማግለል ዝንባሌዎች ያላቸዉ ወገኖችም ቢያስቡበትና ዝንባሌዉ ከወዲሁ መወገድ አለበት እላለሁ። ይህ ፖለቲካ ፓርቲዎች  መታገያ ማእከሎች እንጂ መደበቂያ ምሽግ (ወይም ዋሻ) መሆን የለባቸዉም ይህ ዝንባሌ ካሁን በፊትም ለዚህ ፓርቲ   መስርተዉ ግንባር ቀደም ተሰልፈዉ የ ህ.ወ.ሓ.ት አፈናና  ስቃይ ችለዉ ሲታገሉ የቆዩ ወጣቶች ብቁ አመራሮች በፓርቲዉ በሚታዩት ፀረ ዲሞክራሲ አሰራር አለ በስራ አስፈፃሚዉ ግልፅነት የለም ለአመራሩና ለሌሎች ማግለል አለ በማለት በፓርቲዉ ራሳቸዉአግልላል። እርግጥ ከትግሉ ራስህን ማግለል አይገባም ነበር። በውስጡ ሆነዉ መታገል ነበረባቸዉ። ግን ደግሞ ያለፈዉ አልፏል አሁን ያለዉ አመራር ለዚህ የህ.ዋ.ሓ.ት አባታዊነት ወረርሽኝ በትግል ማስወገድ አለበት። ስለሆነ አረና ትግራይ ከዚህ መማር አለበት። የአባታዊነት ዝንባሌ አብዛኛዉ  በአረና ትግራይ እንዳለ ሆኖ በአሁኑ ጊዜ አመራር ላይ  ወጥቶ ያለ ወጣት ምሁር የፖለቲካ አባል (ከኔ በላይ ላሳር) ለሚል ዝንባሌ አብዛኛዉ አመራረ ለአባታዊነት የሚሸከም ጫንቃ የለዉም። አይችልም ዘመኑ 21ኛ ክፍለ ዘመን ነውና።

ማሳሰቢያ

ለዲሞክራሲ ለፍትህ ለሰብኣዊ መብት ጥበቃ ለህግ የበላይነት ፣ ለነፃነት ለህዝቦች አንድነት የቆማችሁ ሰላማዊ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ከተለጣፊዎችና ሎሌዎች ውጭ የሆናችሁ እንደምናውቀዉና እምደምንመለከተዉ የአብዛኞቻችሁ የፖለቲካና የፖሊሲ ልዩነት የላችሁም። ልዩነታችሁ ያ መጥፎ ኢትዮጵያ ህዝብ እንዲፋለስና እንዲቃቃር ያደረገ  የህ.ወ.ሓ.ት የአባታዊነት ወረርሽኝ ነዉ። ይህ መጥፎ ባህሪ በንቃት አውቀነዉ ስልጣን ማለት መስዋእትነት መሆኑ እንጂ ለቆዳ ክብር ብቻ መሆኑ ተረድተን አባታዊነትን ቀብረን አንድነትን አጥብቀን በመያዝ ካልተራመድን የኣምባገነኑ ህ.ወ.ሓ.ት ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ አገዛዝ እድሜ ከማራዘም አልፎ ከዚህ አምባ ገነኑ ፓርቲ ጎን ተሰልፈን ለኢትዮጵያ ህዝብ ለመቅበር እንደተሰለፍን ያስቆጥራል። አንድነት ስል ግን ከግልሰብ እስከ ብሄር ብሄረሰብ መብት ወደ ጎን በመተዉ  አይደለም ይህ አይሸራረፍም እንዳልሆነና ከላይ ተንሳፍፈዉ ለውጥ የሚመጣ የፓርቲ መሪዎች መግለጫ ስለሰጡ በየሚድያዉ ቃለ-መጠይቅ ቢያደርጉ ህ.ወ.ሓ.ት ለራሱ ለፖለቲካ ፍጆታ ሲል በሚጠራዉ ስብሰባ በቴሌቪዠን መስኮት ብቅ ማለታችሁ ውጤቱ ለህ.ወ.ሓ.ት ጥቅም ነዉ። ስለሆነም ከአዲስ አበባ ጀምሮ እስከ 360 ዲግሪ የኢትዮጵያ ጠረፍ ቀበሌዎች ብትወርዱና የህዝቡን ማእበል ብትፈጥሩ ለዚሁ እንቅስቃሴ የወጣት ብቁ ምሁራኖች  የወጣት ጡንቻ  ብትጠቀሙ ለሰላማዊ ትግል የሚከፈል መስዋእት ይከፈል እንጂ እባካችሁ ይህች ለምለም አገራችን ብቁ ወጣት ምሁራን ወጣቶች ወደ አመራር በማምጣት መላዉ ትውልድ ወደ ሰላማዊ ትግሉ በማዝመት ሰላማዊ ማእበል በማምጣት ሃገራችን ከምጥ እናድናት

እምቢ ለአባታዊነት አንበረከክም!

No comments:

Post a Comment