
ምክር ቤቱ በ2006 እና በ2007 በጀት ዓመት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ክልል ዉስጥ በጥቅሉ ከ2 ሺህ ሄክታር በላይ ቦታ ለመልሶ ማልማትና ማስፋፊያ ስራዎች ለማዋል ያቀደ ሲሆን ቦታዎቹ ለጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ፣ ለንግድ ቦታዎች፣ ለኢንዱስትሪና ለመሳሰሉት በጨረታና በምደባ ስራ ላይ የሚውሉ ናቸው:: ይሄዉ “መልሶ ማልማት” ከሚከናወንባቸው የአዲስ አበባ አካባቢዎች መካከል አራዳ ክፍለ ከተማ’ ደጃች ውቤ ሰፈር፤ አሜሪካን ጊቢ፤ አፍሪካ ህብረት ቁጥር 2 ፣ ቡልጋሪያ ኤምባሲ አካባቢና ለገሃር ዙሪያ ይገኙበታል:: ከዚህ በተጨማሪ ልደታ ክፍለ ከተማና ከዚህ ቀደም በመልሶ ማልማት የኮንደሚኒየም ቤቶች ግንባታ ከተከናወነባቸዉ አካባበቢዎች አንዱ የሆነዉ ጌጃ ሰፈርም የዚሁ የወያኔ የማፍረስ ሴራ ሰለባዎች ሆነዋል።
ባለፉት ሃያ ሁለት አመታት ፕራይቬታይዜሺን ፕሮክትን ጨምሮ ወያኔ የአገርና የህዝብ ልማት እያለ ተግባራዊ ባደረጋቸዉ ፕሮጀክቶች ሁሉ በቀጥታና በተዘዋዋሪ መንገድ ተጠቃሚ የሆኑት የህወሃት አባላት፤ ቤተሰቦቻቸዉና የወያኔ ታማኝ አሽከሮች እንጂ የኢትዮጵያ ህዝብ አይደለም። አሁንም ቢሆን በዚህ “መልሶ ማልማት” በሚባለዉ የወያኔ ዘመቻ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚተርፈዉ ነገር ቢኖር ከመሬቱና ከቤቱ መፈናቀል ነዉ እንጂ ተጠቃሚዎቹ ህወሃትና ግብረ አበሮቹ ብቻ ናቸዉ። ለምሳሌ በ1990ዎቹ በተካሄደዉ የፕራይቬታዜሺን ፕሮጀክት የህዝብና የአገር ንብረት የነበሩ ፋብሪካዎችንና የንግድና የማከፋፈያ ድርጅቶችን በርካሽ ዋጋ ገዝተዉ ዛሬ መጠን የለሽ ትርፍ የሚያጋብሱት “ኤፎርት” በሚል ምህጻረ ቃል በሚታወቀዉ የትግራይ ተራድኦ ድርጅት ስር የተሰባሰቡት የህወሃት ተቋሞች ናቸዉ። ጋምቤላ፤ ኦሮሚያና ኦሞ ሸለቆ ዉስጥ በተካሄደዉ የመሬት ቅርምት በከፍተኛ ደረጃ ተጠቃሚ የሆኑትም እነዚሁ በትግራይ ህዝብ ስም የተቋቋሙት የህወሃት ድርጅቶች ናቸዉ።
No comments:
Post a Comment