Saturday, October 19, 2013

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤ/ክርስቲያን አባቶች መንግስት ቤ/ክርስቲያኑቱን ለማፍረስ ተነስቷል ሲሉ ከሰሱ

ወያኔ በሐይማኖት ተቋማት ላይ የሚያደርሰዉ በደልና ጫና የሰለቻቸዉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርሲቲያን አባቶች የወያኔ አገዛዝ ታሪካዊቷን ቤተክርቲያን ታሪክ አልባ ለማድረግና ለማፍረስ ቆርጦ ተነስቷል ብለዉ መናገራቸዉንና ንግግሩ የአገዛዙን ባለስልጣኖች እንዳስደነገጠ ከአዲስ አበባ የደረስን ዜና አስረዳ። አባቶቹ ይህንን በቤተክርስቲያኒቱ የሺ አመታት ታሪክ ዉስጥ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነዉን በስልጣን ላይ ያለ መንግስትን ፊት ለፊት የመቃወምና የማዉገዝ ንግግር ያሰሙት ሰሞኑን አዲስ አበባ አራት ኪሎ ዉስጥ በሚገኘው መንበረ ፓትሪያርክ የስብሰባ አዳራሽ ዉስጥ በመካሄድ ላይ ባለው 32ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ነዉ። አንድ በስብሰባው ላይ የተሳተፉ አባት ለዝግጅት ክፍላችን በስልክ አንደገለጹት በስብሰባው ላይ ይህ መንግስት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ለማፍረስ እንደተነሳ በተደጋጋሚ ተነግሯል። እኚሁ አባት ጨምረዉ አንደገለጹት በዕለቱ በተደረገዉ ስብሰባ የፌደራል ጉዳዮች የሀይማኖት ክፍል ሃላፊዎች ስለ አክራሪነትና ጽንፈኝነት ገለጻ ለመስጠት የመጡ የአገዛዙ ካድሬዎች ተገኝተዉ አንደነበር ለማወቅ ተችሏል።

በወያኔ ዘመን ኢትዮጵያ ዉስጥ በክርስቲያን ተቋሞችና በክርስቲያኖች ላይ የሚደርሰዉ ግፍና መከራ እየጨመረ መምጣቱን አባቶቹ ተራ በተራ የተናገሩ ሲሆን ፓትሪያሪኩም አባቶች የተናገሩትን በመደገፍ እውነት ነው ይህ ሁሉ መከራና ጫና አለብን በማለት በሊቀ ጳጳሳቱ የተነገረውን ሀሳብ ደግፈዋል። ከመላው አለም የተሰባሰቡ በሺዎች የሚቆጠሩ የሀይማኖቱ መሪዎች በተገኙበት ስብሰባ ላይ የተገኙት የመንግስት ባለስልጣናት የኢትዮጵያን የሀይማኖት ታሪክ አሳንሰዉና አጣጥለዉ ሲያቅርቡ ያዳመጡት አባቶች በቁጣ በመነሳት ለወያኔ አገዛዝ ባለስልጣናት ተገቢዉን ምላሽ ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያን ህዝብ መሬት ነጥቃችሁ፣ ህዝቡንም መሬቱንም የመንግስት ያደረጋችሁት እናንተ ናችሁ፣ ኢትዮጵያዊው ሀብትና ንብረት እንዳይኖረው ያደረጋችሁትም እናንተዉ ናችሁ። የኢትዮጵያን ህዝብ ከዚህ ቀደም የነበሩት መንግስታት ካደረሱበት የበለጠ መከራና ስቃይ ያየዉ በዚህ መንግስት ግዜ ነዉ በማለት አባቶቹ የወያኔን ባለስልጣናት ግራ በጋባና ባስደነገጠ መልኩ ትችትና ወቀሳ አቅርበዋል። ከስብሰባዉ ተካፋዮች አንዱ የሆኑት ብጹዕ አቡነ ቄርሎስ “በአጼዎቹ ዘመን አገራችን ታሪኳ የተከበረ ነበር፤ እናንተም ይህችን አገር ስትረከቡ እስከ ታሪኩዋ ነው . . . ታሪኩዋን አላጠፋችሁም ወይ?” ብለዉ ሲጠይቁ አዳራሹ ዉስጥ የነበረዉ ሰዉ ሁሉ አድናቆቱን በጭብጨባ ገልጾላቸዋል። በዕለቱ ስብሰባ ላይ የተሳተፉት አብዛኛዎቹ የሀይማኖት አባቶች የቤተክስርቲያኗን ታሪክ አዛብታችሁዋል፣ ቤተክርስቲያኑዋንም ታሪኩዋን አጥፍታችሁዋል በማለት ባለስልጣናቱን ወጥረው መያዛቸው ታውቋል። በስብሰባዉ ላይ የሰሜን ወሎ አገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብጹዕ አቡነ ቄርሊዮስ፣ የምእራብ ወለጋ አገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብጹዕ አቡነ ሄኖክ፣ የጋሞ ጎፋ አገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብጹዕ አቡነ ኤሊያስ፣ የምስራቅ ጎጃም ሊቀ ጳጳስ ብጹ አቡነ ማርቆስና የደቡብ ጎንደር ሊቀጳጳስ ብጹዕ አቡነ እንድሪያስ ተገኝተዋል።

No comments:

Post a Comment