Saturday, October 19, 2013

አዲሰ አበባ ዉስጥ ቦምብ ፈንድቶ የሁለት ሰዎች ህይወት አጠፋ

አዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ዉስጥ በተለምዶ ሩዋንዳ ማዞሪያ እየተባለ በሚጠራዉ አካባቢ ባለፈዉ እሁድ ጥቅምት ሦስት ቀን 2006 ዓም ቦምብ ፈንድቶ ሁለት ሰዎች መሞታቸዉን ተገለጸ። ከፌዴራል ፖሊስ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል በተገኘዉ መረጃ መሰረት በቦምቡ ፍንዳታ ሕይወታቸው ያለፈው ሁለቱ ሰዎች በህገወጥ መንገድ ወደ አገር ዉስጥ የገቡ የሶማሌ ዜጎች ሲሆኑ እንደ ፌዴራል ፖሊስ አገላለጽ ፍንዳታዉ የደረሰዉ ሰዎቹ ቦምቡን በሰዉነታቸዉ ዉስጥ ደብቀዉ ወደ ዕላማቸዉ ለመሄድ ሲዘጋጁ ነዉ። ፌዴራል ፖሊስ የሰጠዉን መግለጫ አስመልክቶ ከገለልተኛ አካላት የተሰጠ ሌላ መግለጫ ባይኖርም የሁለቱ ሰዎች ዝግጅትና ለመመሳሰል ብለዉ የያዙት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መለያ እንደሚያመለክተዉ የሁለቱ ሰዎች የጥቃት ተልዕኮ አዲስ አበባ ስቴድዮም ሳይሆን እንዳልቀረ ተገምቷል። ጥቅምት ሦስት ቀን የኢትዮጵያና ናይጀሪያ ቡድኖች ለአለም ዋንጫ ማጣሪያ የተጫወቱበት ቀን ስለነበር አዲስ አበባ ስቴድዮምና አካባቢዉ በዕለቱ በብዙ ሺዎች በሚቀጠሩ የስፖርት አፍቃረዎች ተጨናንቆ እንደነበር የሚታወስ ነዉ።

የአልሽባብ ሽብርተኞች እንደሆኑ የሚነገረዉ ሁለቱ የሶማሌ ዜጎች እጃቸዉ ላይ ከፈነዳዉ ቦምብ በተጨማሪ መጠናቸው ያልተገለጸ ቦምቦችና አንድ ሽጉጥ ከሁለት ካርታ ጥይት ጋር ፣ የፈንጂ ማቆጣጠያና የአደጋ መከላከያ ጃኬቶች፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ማሊያና ቀበቶዎች መገኘታቸውም ተገልጿል፡፡ የአንድ ግለሰብ ሰርቪስ ቤት ተከራይተው ከነበሩት ሁለቱ የሶማሌ ዜጎች ዉስጥ አንደኛው ከ20 ቀናት በላይ የቆየ ሲሆን፣ ሌላኛው ፍንዳታው ከመድረሱ ከሁለት ሰዓታት በፊት የደረሰ መሆኑን ግብረ ኃይሉ ማረጋገጡን አስረድቷል፡፡ ከሶማሊያውያኑ ጋር ቀጥታ ግንኙነት አላቸው የተባሉ ሦስት ተጠርጣሪዎችና የቤቱ አከራይ በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተካሄባቸው መሆኑንም ግብረ ኃይሉ አክሎ ገልጿል፡፡

የወያኔ አገዛዝ የሶማሊያን ግዛትዘልቆ አየገባ በሚፈጽመዉ ጥቃት የተነሳ ኢትዮጵያ ለአመታት ለአልሽባብና ሌሎችም አክራሪ ኃይልች የሽብር ጥቃት የተጋለጠች መሆኗ የሚታወቅ ሲሆን በላፈዉ ወር ኬንያ ናይሮቢ ዉስጥ ለደረሰዉ የሽብር ጥቃት አልሽባብ ሀለፊነት ከወሰደ በኋላ ግን ኢትዮጵያ የሚቀጥለዉ የአልሽባብ ጥቃት ሰለባ ትሆናለች የሚል ከፍጠኛ ፍራቻ አንዳለ ብዙዎች ተናግረዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ቦሌ ዉስጥ እንደዚያ አይነት ከፍተኛ የቦምብ ፍንዳታ ደርሶ ፖሊስ አደጋዉ ወደ ደረሰበት ቦታ የመጣዉ ከ30 ደቂቃ ቆይታ በኋላ መሆኑን የገለጹት የአካባበዉ ነዋሪዎች ስጋታቸዉን ገልጸዋል። እንደ ነዋሪዎቹ አባባል አደጋዉ ደረሰዉ በተወሰነ ቦታ መሆኑና ተጠርጣሪዎቹም ወዲያዉ ስለሞቱ ነዉ አንጂ እንደ ኬንያው ዌስትጌት ጥቃት ቢሆን ኖሮ ፖሊስ የሚደርሰዉ ብዙ ሊተርፍ የሚችል ሰዉ ከሞተ በኋላ ነበር በማለት ብዙ የአካባቢዉ ነዋሪዎች በፖሊስ ላይ ያላቸዉን ስጋት ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment