ኔልሰን ማንዴላ የነፃነት ትግልን በግንባር በመሰለፍ መርተዋል። ኢትዮጵያ ድረስ በመምጣት ወታደራዊ ሥልጠና ወስደው ዘረኛዉን የፕሪቶሪያ አገዛዝ በመሣሪያ ታግለዋል። የእሳቸው ጠመንጃ ማንሳት ለበርካታ ወጣት ታጋዮች አርዓያ ሆኗል። እስር ቤት በቆዩባቸው 27 ዓመታት ደግሞ የድርጅታቸውንና የትግሉን አመራሩ ለጓዶቻቸው በመተው እርሳቸው ለነፃነትና ለእኩልነት በመታሰርና ስቃይን በመቀበል ትግሉን መርተዋል። በዚህም ምክንያት በትግል ሜዳም በእስር ቤትም መሪ እንደሆኑ የዘለቁ ታላቅ አፍሪቃዊ ናቸው።

ኔልሰን ማንዴላ ታላቅ የነፃነት አርበኛ፣ ታላቅ የለውጥ አራማጅ፣ ታላቅ መምህር እና ታላቅ የእርቅ ሰው ነበሩ። ዛሬ ዓለም እኚህን ታላቅ አፍሪቃዊ አጣች።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በኔልሰን ማንዴላ ሕልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ይገልፃል። ከእንግዲህ ማንዴላን የምናስባቸው ከእሳቸው ተሞክሮ የምንማረው ሲኖር ነው። በዘረኝነት እየተጠቃን ላለነው ኢትዮጵያዊያን የማንዴላ ትምህርት ሕያው ሊሆን ይገባል።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ዘረኝነትን በጽናት የመታገል ሆኖም ግን ይቅር ባይ የመሆንን እሴቶች ተግባራዊ በማድረግ ማንዴላ በሕይወት ቢለዩንም በመንፈስ ሁሌም አብረውን እንዲኖሩ እናድርግ ይላል።
የግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ህዝብ ግንኙነት
No comments:
Post a Comment