Saturday, November 2, 2013

ደብረማርቆ ዩኒቨርስቲ ዉስጥ ለተነሳዉ አመጽ የዩኒቨርሲቲዉ አስተዳደር ኢሳትን መኮነኑ ተሰማ!

ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ አዲስ ያወጣዉን ፀረ ህዝብ መመሪያ ተከትሎ የደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ አዲስ የአለባበስ ፤ የአመጋገብና የአምልኮ ስርዓት ህግ ማውጣቱን በመቃወም የዩኒቨርሲቲዉ ተማሪዎች የረሃብ አድማ መጀመራቸዉን የዩኒቨርሲቲዉ አስተዳደር ገለጸ። ከዚህ በተጨማሪ አዲስ ከወጣዉ መመሪያ ዉጭ ዩኒቨርሲቲዉ ለተማሪዎች የመደበዉ የምግብ ፍጆታ መጠን እጅግ በጣም ዝቅተኛ ነዉ በሚል የተማረሩት የዩኒቨርሲቲዉ ተማሪዎች አመጽ መጀመራቸዉን የዩኒቨርሲቲዉ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ንጉሴ ምትኩ መናገራቸዉ ታዉቋል። ዶ/ር ንጉሴ ምትኩ ከዚሁ ጋር አያይዘዉ እንደተናገሩት ተማሪዎቹን ቁርስ፣ ምሳና እራት ለመመገብ የሚኒስትሮች ምክር ቤት የተፈቀደው የቀን በጀት 12 ብር ብቻ ነዉ ካሉ በኋላ በደብረ ማርቆስ ከተማ 12 ብር ከአንድ ሻይና ዳቦ በላይ መግዛት እንደማይችል ተናግረዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ኢሳት ቴሌቪዥን ያናገራቸዉ አንዳንድ የዩኒቨርሲቲዉ ተማሪዎች ደብረ ማርቆስ ዉስጥ ለአንድ ተማሪ በቀን 12 ብር ለምግብ መመደብ ተማሪዎችን በረሃብ ለመጨረስ ከመሞከር ተለይቶ አይታይም ብለዋል።

የዩኒቨርሲቲዉን ተማሪዎች ጥያቄ ትክክለኛነት ያረጋገጡት የደብረማርቆስ ዩኒቨርስቲ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ንጉሴ ምትኩ ከመንግስት ፈቃድ ውጭ በሚልየን የሚቆጠር የበጀት ድጎማ እያደረግን ተማሪዎችን ለመመገብ ጥረት አድረገናል ብለዋል። ይህንን ሀቅ ሳይደብቁ የተናገሩትና የተማሪዎቸን ችገር በሚገባ የተረዱት ዶ/ር ንጉሴ የደብረማርቆስ ዩኒቨርስቲ ዉስጥ የተነሳዉ የተማሪዎች አመጽ ምክንያቱ አሰገዳጅ ህጉና የምግብ ማነስ ሳይሆን ኢሳትና ሌሎች ሃይሎች ያደራጁት አመጽ ነዉ ብለዉ መናገራቸዉ ብዙዎችን አስገርሟል።ይሀንን የዩኒቨርሲቲዉ ፕሬዚዳንት ኢሳት ላይ የሰነዘሩትን ክስ የሰማ አንድ የዩኒቨርሲቲዉ ተማሪ አመጽ፤ ተቃዉሞና ህዝባዊ እምቢተኝነት ኢትዮጵያ ዉስጥ በየቦታዉ የሚታይ ከስተት መሆኑ እየታወቀ ፕሬዚዳንታኢን የደብረማርቆሱን አመጽ በኢሳት ላይ ማሳበባቸዉ የሚያሳየን የአዋቂ አላዋቂነትን ነዉ ብሏል።

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ዉስጥ የተቀሰቀሰዉ አመጽ በስድስት ህንጻዎችና በሶስት የትራንስፖርት አገልግሎት በሚሰጡ አምቡላንሶችን ላይ ከፍተኛ አጉዳት ማድረሱ የታወቀ ሲሆን አመጹን ለመቆጣጠር የፌደራል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ በተማሪዎች ላይ ድብደባ ፈጽሟል፡፡ ዬዩኒቨርስቲው መሪዎች የአካባቢው ነዋሪዎች ለዩኒቨርሲቲዉ አመጽ ድጋፍ ሰጥተዋል የሚል ስሞታ ያሰሙ ሲሆን ነዋሪዎች በበኩላቸው ተማሪዎች እየራባቸው ሲወድቁ በዝምታ አለመመልከት የዜግነት ግዴታችን ነዉና እርደታ ለመስጠት ተገድደናል ብለዋል።

No comments:

Post a Comment