Wednesday, November 13, 2013

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ)በሳውዲ አረቢያ በዜጎች ላይየሚፈጸመው ኢሰብአዊ ድርጊት አውግዞ በቅርቡ በሚጠራው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ሕዝቡ በነቂስ በመውጣት በወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና በደል በመቃወም ድምፁን እንደዲያሰማና ወገናዊ አጋርነቱን እንዲያሳይ መድረክ ጥሪ ቀረበ

የሳውዲ መንግስት በኢትዮጵያውያን ዜጎቻችን ላይ እየፈፀመ ያለውን ኢሰብኣዊነት አጥብቀን እናወግዛለን!!!
--------------------------------------------------------------------
መድረኩ በጠራው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ህዝቡ በነቂስ እንዲወጣ ጥሪ እናቀርባለን!
-----------------------------------------------------------
ከኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) የተሰጠ መግለጫ

ሰሞኑን በሳውዲ አረቢያ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ዜጎቻችን ላይ እየተፈፀመ ያለው ድብደባ፣ ግድያና በጅምላ ማጎር ከኢሰብአዊነቱም በላይ የሳውዲ መንግስት ለዜጎች ያለው ክብር በጣም ዝቅተኛ መሆኑን የሚያሳፍር ድርጊት ነው፡፡ በኢትዮጵያዊነት ክብር ላይ የተሰነዘረ ጥቃትም ነው፡፡ በኢትዮጵያውያን ሉአላዊነት ላይ የተፈፀመ ወንጀል ሲሆን ዜጎቻችን በጭካኔ ሲገደሉ፣ ሲፈነከቱ ሲታጎሩና ሲገረፉ ማየት አንገት ያስደፋል፡፡ በአንድ አፋኝ ስርዓት ውስጥ የምንገኝ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከዚህ በላይ ምን እንላለን?

ይህ በሳውዲ መንግስት ደፋርና ኋላ ቀር የሆነ ድርጊት የኢህአዴግን መንግስት የዲፕሎማሲ ተፅዕኖ መፍጠር ድክመት ከመግለፁም በላይ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ያለውን ደንታቢስነት ይመሰክራል፡፡ ድሮስ በመልካም አስተዳደር እጦት ፍትህን ከተነፈገ፣ በሙስና ከተጨማለቀና በፖለቲካ ስልጣን ለመቆየት ቆርጦ ከተነሳ የስልጣን ኃይል ምን ይጠበቃል? ዜጎችንና ሃገሪቱን ያስደፍደራል፣ የሉኣላዊነትን ክብር ያስነካል፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ የኢህአዴግ መራሹ መንግስት የተሳሳተ ፖሊሲ እየፈጠሩ ካሉት ችግሮች አንዱ ማህበራዊ ቀውስ መሆኑን ገጠዋል፡፡ ዜጎች ተስፋቸው ጨልሞ እየታያቸው ነው፡፡ ተስፋ ያጣ ዜጋ ተስፋ ይቆርጣል፡፡ በተወለደበት ቀየና ሃገር የኑሮ እምነትና ዋስትና የሌለው ዜጋ ሞት እየሸተተውም ይሰደዳል፡፡ በአገራችን ስራ አጥተው ስራ ፍለጋ ሲንከራተቱ በሰው ሃገር በረሃ ሰብአዊ ክብራቸው ተዋርዶ ህይወታቸው ያለፉ ዜጎችን ዜና መስማት በኢህአዴግ አገዛዝ የተለመደ ሆኖአል፡፡ በጣም የሚያሳፍረው ኢህአዴግ እነዚህን ዜጎች “ህገ ወጥ ስደተኞች “ በሚል ፍረጃ ለመብታቸው ለመቆም ቁርጠኝነት የሚጎድለው መሆኑም ጭምር ነው፡፡

መድረክ ዜጎቻችን የሚሰደዱበት የተሻለ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ፍትህ ፍለጋ እንዲሁም አሰቃቂ የሆነውን የአንድ ፈላጭ ቆራጭ አምባገነናዊ ፓርቲ የፖለቲካ አስተዳደር ሽሽት መሆኑን ይገነዘባል፡፡


በተደጋጋሚ እንደገለፅነው ዜጎቻችን ወደ ደቡብ አፍሪካ፣ መካከለኛው ምስራቅና አውሮፓ ለመሰደድ በባህር፣ በበረሃና በጫካ ውስጥ ተቀጥፈው ቀርተዋል፡፡ የዚህ አንገት አስደፊ ዜና ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ እንጂ ሲቀንስ አይታይም፡፡ በለስ ቀንቷቸው ባህሩን፣ በረሃውንና የዱር አውሬውን አልፈው ማረፊያዬ ብለው ያሰቡበት አገር የሚደርሱትም ሌላ ግፍና በደል ይጠብቃቸዋል፡፡ ሃገራዊ ውርደትና ሞት ከተበላሸ ስርዓትና ፖሊሲው የሚፈጠር እንደመሆኑ የችግሩ ምንጭ ኢህአዴግ መሆኑን እናምናለን፡፡

መድረክ ይህ ሁሉ ውርደት የሚደርቀው የችግሩ ምንጭ ሲነጥፍ ነው ብሎ ያምናል፡፡ የችግሩ ምንጭ ደግሞ ኢህአዴግ ነው፡፡ ስለሆነም በዚህ ፓርቲና መንግስት ላይ ህገ - መንግስታዊና ሰላማዊ የሆነ ተፅኖ በመፍጠር ስርአቱን መቀየር ወሳኝ መሆኑን ያምናል፡፡ ህዝቡ አንድነቱን በማጠናከር በጋራ እንዲንቀሳቀስ ጥሪውን በድጋሚ ያቀርባል፡፡

በሳውዲ አረቢያ የመንግስት ኃይሎች በዜጎቻችን ላይ በተፈፀመው ሰብአዊነት የጎደለው ድርጊት ላይ የመድረክ አቋም፡-


  • በዜጎቻችን ላይ እየተፈፀመ ያለው የሰብአዊ መብት ጥሰት በአስቸኳይ እንዲቆም፤
  • ለተፈፀመው አስነዋሪ ወንጀል ተጠያቂው አካል ተለይቶ ለህግ እንዲቀርብ፣ ለተጎጂዎችም ካሳ እንዲከፈል፤
  • ለተፈናቀሉ ዜጎች የአስቸኳይ ጊዜ ርዳታና መስራት የማይችሉት ተለይተው በክብር ወደ ሃገራቸው እንዲመለሱ፡፡ መስራት የሚችሉና ፈቃድ የሚያገኙቱ ሰብአዊ ክብራቸው ተጠብቆ እንዲኖሩ እንዲረግ፤

የኢህአዴግ መንግስት በጉዳዩ ላይ ለሕዝብ ሰፊ ማብራሪያ እንዲሰጥና ከሳውዲ መንግስት ጋር ያለውን ሁለንተናዊ ግንኙነት በመፈተሽ ጠበቅ ያለ አቋም እንዲወስድ እንጠይቃለን፡፡ በዚህ ድርጊት መባባስ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትርና በሳውዲ የኢትዮጵያ አምባሳደር /ቆንስላ ጽ/ቤት ተጠያቂዎች ሲሆኑ ይህም ስልጣን የሚሰጠው በችሎታና ለወገን ባለው ተቆርቋሪነት ሳይሆን በፓርቲ ታማኝነት እንደሆነ እየመሰከረ ያለ ጉዳይ መሆኑን ነው፡፡

አለምአቀፍ የሰብአዊና የዲሞክራሲ ተቋማትም ይህን አሳፋሪ ተግባር ህግና መንግስት ባለበት አገር እየተፈጠረ መሆኑን እንዲያስተጋቡ፡፡ ጉዳዩን ለአለም እያደረሱ ያሉትን ታላላቅ ሚዲያዎችን በዚሁ አጋጣሚ ለማመስገን እንወዳለን፡፡ መድረክ ድርጊቱን ለመኮነን በቅርቡ አዲስ አበባ በሚገኘው የሳውዲ አረቢያ ኤምባሲ ፊት ለፊት ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግና ለማስተባበር ወስኗል፡፡ ቀኑን በጥቂት ቀናት ውስጥ የሚያሳውቅ ሲሆን አጠቃላይ ሕዝቡ፣ ደጋፊዎችንና አባላት፣ በአገር ውስጥ የምትገኙ የተቃውሞ ጎራው የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ነፃ ነን የምትሉ የሲቪክ ማህበራትና የኢህአዴግ አባላት ሁሉ በሚገለጸው ዕለት፣ ቦታና ሰዓት በመገኘት ድርጊቱን ጨዋነት በተሞላበት ሁኔታ ለማውገዝ ትገኙልን ዘንድ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

ከኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ)
ኅዳር 04 ቀን 2006 ዓ.ም

No comments:

Post a Comment