Friday, October 30, 2015

ከሰንደቁ ፊትም በኋላም (ከሠራዊቱ ድምፅ ራዲዮ)

አንደሚታወሰዉ ባለፈዉ አመት እንደ አዉሮፖዉያን ዘመን አቆጣጠር በዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ ነዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያዉያን ሰልፈኞች መስከረም 29ቀን 2014 ዓም እጅግ ሥርአታዊ ዲሲፕሊን የተሞላዉ ጥያቄ አንግበዉ ወደ ኢትዮጵያ ኢምባሲ ሄደዉ ነበር። በሰላማዊ ሰልፎች የተለመደዉን የገማ እንቁላል፤የበሰበሰ ቲማቲም፤ቆመጥና ድንጋይ እንደመሣርያ ይዘዉ አልሄዱም። በእለቱ የተቃጠለ የወያኔ ንብረትም ሆነ የተዘረፈ የወያኔ ሀብት አልነበረም። ያ ተግባር አሁን በሥልጣን ላይ ያለዉ የወያኔ ዘረኛ አገዛዝ የተካነበት ሞያ ስለሆነ ወደዚያ የተሰማራ አልነበረም። በዚያ ሠልፍ ላይ የተሰማሩ ወጣት ኢትዮጵያዉያን ልባቸዉ ሲነድ የቆየበትን አንድና አዲስ አይነት እንቅስቃሴ አሳይተዋል። ይኸዉም የኢትዮጵያ ሕዝብ ለአያሌ ዘመናት የጀግንነቱ ማረጋገጫ፣የነፃነቱ ምልክትና የተስፋዉ ፅኑ ማስረጃ አድርጎ ሲመለከተዉ የኖረዉን ሰንደቅ አላማ በግቢዉ ዉስጥ ለማዉለብለብ ችለዋል። “ወድቃ የተነሳችዉ” ሰንደቅ ዓላማ የፍትህና የርትህ ተስፋ መሆንዋን ሕዝቡ የሚቀባበለዉ እዉነታ ነበር። አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ሰንደቅ ዓላማችንን እየተመለከተ ወራሪዉን የኢጣልያ ሠራዊት የመታዉን የአድዋ መቶ ሺህ ሠራዊት የምናስታዉስበትና ለጥቁር ሕዝብ ሁሉ የአርነት አርማ አድርገን የምንቆጥረዉ ነዉ። ይህቺ ሰንደቅ ዓላማ ከሃምሳ በላይ ለሆኑ የአፍሪካ አገሮች ነፃነት አስተዋፅኦ አድርጋለች። ከሰላሳ የሚልጡ ሰንደቅ ዓላማዎች የዚችን ታሪካዊ አገር አርማ የተቀበሉና የተከሉ ናቸዉ።

አንድ አገር የሚደፈረዉ ብሄራዊ አርማዉና የነፃነት መታሰቢያዎቹ በተነኩ ወቅት ነዉ። ከዉጭ የሚመጣ ወራሪ ኃይል መከሰቻዉ የማንነቱ ማስረጃ የነፃነቱና የጀግንነቱ ማረጋገጫና የብሄራዊ ኩራቱ ምልክት የሆነዉ እንደ ሰንደቅ ዓላማ ያለ የክብር አርማ ሲረገጥ ነዉ። የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ የአሸናፊነትና የጀግንነት ተቀባይነት ያገኘዉ በቀጥታ በተዘመተበት መንግሥት ጭምር ነዉ።

የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የአሸናፊነትና የጀግንነት ተቀባይነት ያገኘዉ በቀጥታ በተዘመተበት መንግሥት ጭምር ነበር። ስለሆነም ኢጣልያና እንግሊዝ ኤርትራ ዉስጥ ከስልሳ አመታት በላይ ሲቆዩ በደብረ ቢዘን በኦፊስየል የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ሲዉለበለብና እያንዳንዱም ኤርትራዊ ኢትዮጵያዊ ሰርግና ልደት ክርስትናና ሞት በዚችዉ ሰንደቅ ዓላማ ሲያጌጥ በመኖሩ ነበር።

በኢሳት ቴሌቪዥን ላይ አንድ ኢትዮጵያዊ እንደገለጡት ይህንን ሰንደቅ ዓላማ ሕዝቡ ብቻ ሳይሆን ግመሎቹ ፈረሶቹና በቅሎዎቹ ጭምር የሚያዉቁትና የሚያከብሩት ነበር። የኢሳዉ ባላባትና መሪ ደጃዝማች ኡጋዝ ሃሰን እንደጠቀሱትም “ግመሎቹ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ሲያዩ ሸብረክ ብለዉ ያሳልፉታል” ሁላችንም የትናንት ትዉልዶች ይችን ሰንደቅ ዓላማ በተማሪነት ዘመናችን በጠዋት መዝሙራችን አዉለብልበን ማምሻዉ ላይ አዉርደን አጣጥፈንና አክብረን እናድራለን። በመንገድ ላይ ሆነን ሰንደቅ ዓላማችን ሲከበር ቆመን አብረን እናከብራለን።

የዚችን አገር አንድነት ለመጠበቅ ከመላዉ ኢትዮጵያ የተዉጣጣ የአገር ዳር ድንበር ጠባቂ የሆነዉ የመከላከያ ሠራዊታችን ሰንደቅ ዓላማችን ሥር ተንበርክኮ ቃልኪዳን ሲገባ ኖሯል። ለዚች የነፃነት ዓርማ ክብር ሥፍር ቁጥር የሌለዉ የመከላከያ ሠራዊታችን ሕይወቱን ሰዉቶላታል።ቀባሪ ያጣዉ ጀግና አሁንም ለተተኪዎቹ ትዉልዶች ልዩና ዘላለማዊ ጥሪዉን እያቀረበ ነዉ። ካስከበረዉ የናቱ ማሕፀን ሆኖ “እኔ የሞትኩላትን አገር አንተም የማስከበር ግዴታ አለብህ” እያለ አደራህን እያሳሰበህ ነዉ። የጎበናና ከአብራኩ የተከፈለዉ አበበ አረጋይ፣ ሃይለማርያም ማሞ፣የአሉላ አባነጋ፣ የበላይ ዘለቀ፣ የበቀለ ወያ፣የአብዲሳ አጋ፣ የቶላ በዳኔ ነፍሶች ጥሪ ሊሰማህ ይገባል።


በዚህ አንፃር የተከበረችዉንና በጀግኖች ደም የቆመችዉን ሰንደቅ ዓላማ ዛሬ በስልጣን ኮርቻ ላይ የተፈናጠጠዉ የትግሬ ነፃ አዉጪ ነኝ ብሎ ራሱን የሚጠራዉ የነፍሰገዳዮች ቡድን ምንኛ እንዳሳደፋት፣የኢትዮጵያን መከላከያ ሠራዊት ደም መናኛ እንዳደረገዉ ዛሬ ልንተሳሰበዉ ይገባናል። የእድል መዛባትና የጊዜ መገጣጠም አመችቶት አረመኔዉ መለስ ዜናዊ በጠቅላይ ሚኒስትርነት አዲስ አበባ ሲገባ አገሪቷን በመናቅና ሕዝቡንም በመፀየፍ መልክ የተናገረዉን መድገም አስፈላጊ አይመስለንም። ያንን ግፍ በድል እስከምናርመዉ ድረስ የሁላችንም የልብ ቁስል አይሽርም። ስለዚህ የሁላችንም ትግል ይዘት ለዚያች ብሔራዊ አርማችን ድል አድራጊነትና ብሔራዊ ተሃድሶ ነዉ።

No comments:

Post a Comment