Wednesday, February 4, 2015

አብዮት መንታ ነው (ሄኖክ ታደሰ ጆሃንስበርግ)



“የአብዮት ያለህ!”፥ አትበሉ ባ’ገሬ፣
በአብዮት መሃል፥ አብዮት አይጠሬ፣
ምስጋና ቢስ ትውልድ፥ ሆነነው ነው እንጂ፣
የግፈኛን ቀብር፥ የምናበጃጅ፣
የሚሞቱልንን፥ የደም ዋጋ ንቀን፣
በአብዮት መሃል፥ ካ’ብዮት ርቀን፣
በአርበኞች መሃል፥ ባ’ርበኝነት ስቀን…

“ደሃ ህዝብ አስፈጁ”፥ ስንል ተሰምተናል፣
“አመሉ ሲታወቅ”፥ ብለን አድንቀናል፣
‘ያስፈጀው’ ሲወገዝ፥ ፈጂውን ትተናል፣
አህያ እየፈራን፥ ዳውላ መ’ተናል።

ልንገርህ ወገኔ፥

አብዮት ሁለት ነው፥ መንታ ነው ፍጥረቱ፣
እርግጥም አብዮት፥ ስም ያገኘበቱ፣
በዳዮችን ሲጥል፥ ስርአት ሲዘረጋ፣
ሙሉ ሥም ያገኛል፥ አቢዮት እዚህጋ።
ነገር ግን ሲመታ፥ በበዳይ ፍላጻ፣
አቢዮት ተሽሮ፥ ይባላል አመጻ።
“አብዮት የለም” አንበል፥ አብዮት አለን እኛ፣
ግዞት ቤቱ የሞላው፥ በአብዮተኛ።

“There are accepted revolutions, revolutions which are called revolutions; there are refused revolutions, which are called riots.” — Les Miserables/ Victor Hugo

No comments:

Post a Comment