Tuesday, November 4, 2014

የግንቦት 7 ንቅናቄ በጣሊያኗ መዲና ሮማ ታላቅ ህዝባዊ ስብሰባ አካሄደ

ባሳለፍነው እሁድ የግንቦት 7 ንቅናቄ በጣልያን ዋና ከተማ ሮማ ያካሄደው ህዝባዊ ስብሰባ በስኬት ተጠናቀቀ። በህዝባዊ ስብሰባው ላይ በሮማ እና አጎራባች ከተሞች የሚኖሩ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የተሳተፉበት እንደነበር ተመልክቷል። የንቅናቄያችን ም/ ሊቀመንበር አቶ አበበ ቦጋለ በህዝባዊ ስብሰባው ላይ በክብር እንግድነት ተጋብዘው የተገኙ ሲሆን አቶ አበበ ቦጋለ ከኢትዮጵያውያን ጋር ሰፊ ወቅታዊ አገራዊ ውይይት በማድረግ የንቅናቄያችንን የትግል ስልቶች ማለትም ህዝባዊ ተቃውሞ፤ ህዝባዊ አመጽና፤ ህዝባዊ እምቢተኝነት በተመለከተ ሰፊ ገለፃ ካደረጉ በኋላ ለተግባራዊነታቸው እየተደረገ ያለው ሰፊ ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ሲሉ ጥሪ ማቅረባቸው ታውቋል። አቶ አበበ ከተሳታፊዎች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ማብራሪያ መስጠታቸውም ታውቋል።

በህዝባዊ ስብሰባው ላይ የተገኙት ኢትዮጵያውያን ንቅናቄው አሁን ላይ የደረሰበት የትግል ደረጃ እንዲሁም በንቅናቄው የተተገበሩትን የትግል ስልቶች በማድነቅ፤ የግንቦት 7 ንቅናቄ የጉጅሌው ወያኔ አገዛዝን ለመገርሰስ የጀመረውን ትግል ከዳር ለማድረስ የሚጠበቅባቸውን ማንኛውም አይነት መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያውያኑ በገንዘብ፤ በሰው ሃይልና በዕውቀት ረገድ ድጋፍ በማድረግ ከንቅናቄው ጎን እንደሚሰለፉ ቃል ኪዳን መግባታቸውም ተመልክቷል። በህዝባዊ ስብሰባው ላይ የቀረበላቸውን የተቀላቀሉን ጥሪ በመጠቀም ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ኢትዮጵያውያን በአባልነት እንዲሁም በደጋፊነት በመመዝገብ ግንቦት 7 ትን መቀላቀል መቻላቸውም ታውቋል።


በስብሰባው ላይ በጠላት እጅ ወድቀው የሚገኙት የንቅናቄያችን ዋና ፀሐፊ የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ሥራዎች በስፋት የተወሱ ሲሆን የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስራዎች ኢትዮጵያውያኑን በቁጭት ያስነቡ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል። ኢትዮጵያውያኑ ከፍተኛ ገንዘብ እየተደረገ ላለው የነፃነት ትግል ድጋፍ ይሆን ዘንድ መለገሳቸውም ታውቋል። በመጨረሻም ለአገር መከላከያ ሰራዊት፤ ፖሊስ እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ እየተደረገ ባለው የሞት ሽረት የነፃነት ትግል ከግንቦት 7 ጎን ይሰለፉ ዘንድ ጥሪ ከቀረበ በኋላ ስብሰባው መጠናቀቁ ተመልክቷል።

No comments:

Post a Comment