Sunday, December 21, 2014

" ኦ ባህር ዳር ! "

ሀገር ይዘን ፣ ሀገር አጥተን
ሰው ሞልቶ ፣ ሰው ጠፍቶብን
ባህር ወደን ፣ ባህር አጥተን
ባህር ይዘን ፣ ውሃ ጠምቶን
እውንት ይዘን ፣ ውሸት ተብለን
ድህነትን አቅፈን ፣ አድገት እያልን
ሰብዕናውን ሳናስቀድም ትተን
በእድገታችን ልማት ተመጻድቀን
የመናገር መጻፍ ፣ መቃወሙን
ፈጣሪ የሰጠንን መበት ተነፍጎን
ፈጣሪ አያለ ፣ ሰው አምልከን
ሹም እያለ ፣ ፍትህ ርቆን
የባህር ዳሩ ማህበል አይሎብን
ሰው ተጎዳ ፣ ሀዘን ጎዳን ...

እናማ!

አዝነን ከፍቶን፣ ጊዜ ጎድሎብን
የሞተ ቀባሪ ፣ ከንፈር መጣጭ ሆነን
ጨንቆን ጠቦን ፣ ፍርሃት አዋርዶን
የቁርጥ ቀን ልጆችን ግንባር እያስመታን
የቆሙለትን ፍትህ ጥያቄ እያጥላላን !
እዚህ ደርሰን እንዲህ ሆንን ...

ለሆዳችን አድረን ፣ሰብዕናን አስረግጠን
እውነትን በገሃድ መጋፈጥ ገዶን
ውሸትን የመቃወም ወኔ ተሰልበን
በአንቶ ፈንቶ በብርቅርቅ ህይወት ተታለልን !

ዛዲያማ ...

ራሳችን ሳንሆን ፣ ሳናዳምጠው ውስጣችን
መሄጃ መድረሻ ፣ ጠፍቶን መንገዳችን
ለፍትህ ሳንተጋ ፣ ለመመጻደቁ ተግተን
ፈጣሪን ሰው አድርገን ፣ ሰውን እያመለክን
የማይጨበጥ የማይሆነውን እያወራን
በማይዳሰስ ተስፋ ፣ አመታትን ገፋን !


አንገታችን አቅንተን እንባችን እያዘራን
ይታረቀን ዘንድ አንድየን እየለመንን
"ኤሎሄ ኤሎሄ! " ብለን እንጮሃለን!
ሳንሰራ ይሰማን ያየን መስሎን !
ሰው መሆን ገዶን ፣ግፍን መቃወም ተስኖን
"ኦ ባህር ዳር " እንላለን !
ግፍ በዝቶብን ፣ የሰው ደም እየገበርን !
አዎ! "ኦ ባህር ዳር " እንላለን !

( ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም በባህር ዳር ሁከት ተነስቶ ለፈሰሰውን የወገን ደምና የእኛን ኑሮ አውጥቸ አውርጀ ትዝብቴን በስንኝ ቋጥሬ ለተጎዱት ማስታወሻ ትሆንልኝ ጻፍኳት ! በግፍ ህይዎታቸው ያለፉትን ወገኖች ነፍስ ይማር ! )

ነቢዩ ሲራክ

ታህሳስ 11 ቀን 2007 ዓም

No comments:

Post a Comment