Wednesday, July 23, 2014

ይድረስ ለመላ ኢትዮጵያ ህዝብ – ኢትዮጵያ! ሸክህምህን አራግፍ! (ሥርጉተ ሥላሴ)


እጅግ የምትናፍኝ፤ የምሳሳልህ ክብሬና ማዕረጌ ሰፊው የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ!

2005 እንዴት ነህ ብዬ ለመጠዬቅ አቅም የለኝም። መከራ ባዘራ ሰቀቀን፣ ስቃይ በከተመበት ኑሮ፣ ራህብ ትንፋሹ ባደረገ ህይወት፣ መገለልን አብዝቶ በከዘነ አዬር፣ መቀጥቀጥን ውቅራቱ ባደረገ ማዕልት፤ ፍርኃትን በሸመተ ድቅድቅ ሌሊት እንዳላህ እረዳለሁ።

ዛሬ በአንድ የጎሳ አንባገነን አስተዳደር በትግራይ ነፃ አውጪ ድርጅት በአድሎ መከትከቱ፣ የቀደመው ማንንት ሁሉ ተቀዶ ማፍሰሱ፣ የነፃነት ትንፋሽነት በጦር መወጋቱ፤ በባዕት በባይተዋርነት ሁሉን ችሎ መተከዙ እስከመቼ? ሸክሙ የሚራገፍበት ሁኔታ እንዴት ይሰናዳ? እንዴተስ ቆርጠህ ግፍና በደሉን ማረገፍ ተሳነህ?

በሰላማዊ ትግል የተሰለፉ ልጆችህ በተገኙበት ቦታ እዬታደኑ የአራዊት ፍትህወት መወጣጫ፤ የቂም መደቆሻ፤ የበቀል ማወራረጃ እዬሆኑ ዕንባን ሰንቆ ቀንን ማስለቱስ እስከመቼ ትቀጥልበት ይሆን?

መቼ ይሆን ይህ የመንፈስ መጋኛ የሆነ ዘር አጥፊ፤ ታሪክ ገዳይ፤ ትውልድን ደምሳሽ የዞግ ሥርዓት በቃህን በማለት ቁጣህን በህብረት የምትገልጠው? ከተቆጡትስ ጋር ተቀላቅለህ በስፋት ወጥተህ ፍዳህን – መከራህን ለዓለም አደባባይ የምታሳዬው ሰላማዊ የንቅናቄ የቁጣ እሳትህን መቼ ይሆን የምታነደው? ቀጠሮው እስከመቼ ነው?

ሴት ልጆችህ ለአራዊት እየታደኑ መጫወቻ ሆኑ። ወንድ ልጆችህም የግብረ ሰዶም ማርኪያ ሆኑ። ኢትዮጵያ ላይ የነነዌ ቀን እንዲህ ተፈቅዶለት እዬተጠበቀ ነው። የፈጣሪ ቁጣ ሲመጣ ሞገዱ አንተን ንዑዱን ከኃጢያተኛው ሳይለይ ይጨመርኃል። ስለዚህ ይህን የገማ ሥርዓት ከሥሩ ለመንቀል ከልብህ ሆነህ ሥርዓትህን ጠብቀህ የጠላኸው መሆኑን  በአንደበትህ እርግጡን ንገረው። ወያኔ ሲፈጠርም የአንተ አይደለም። አሲድ – ዲዲቲ ነው። መርዝ ነው ወያኔ።

እርግጥ ነው ጥቂቶች በልተው ያድራሉ። ውጭ ሀገር ልጆች ያላቸው። እነሱም እዬታፈኑልህ ነው። ተሰደውም ሰላም አልሰጣቸውም ሽፍታው ወያኔ። ስደት ላይ ያሉ ልጆችህ ሰላም አግኝተው እንደፈለጉት መንቀሳቀስ፣ ሠርተው ወጥተው መግባት እስካልቻሉ ድረስ ነገ ውጪ ሀገር ልጆች ያላቸው ቤተሰቦችም ቢሆን ጉሮሯቸው ይታነቃል። አፋኙ ወያኔ የውንብድና ተግባሩ ሆነ የማሳደድ ሥራው ከመቼውም በሰላ ሁኔታ በመሰሪ ደባ በውጭ ሀገርም እዬከወነው ይገኛል።


ሌላም ነገር አለ ሽፍታው ወያኔ ኑሮው ከተገነባበት አንዱ ልጆችህ በሚሰዱት የውጭ ምንዛሬ ስለሆነ ውጭ ያሉት ልጆችህ ተስማምተው ተቆራጩን ቢያቆሙስ? ሁሉም ይከረቸማል። በቀል የጠማውን ሽፍታ ለማምከን አንዱ የሰላው መንገድ ይህ ብቻ ነውና።

እንዲህ ወያኔ ልጆችህ በሄዱበት በተሰደዱበት ሀገር እንኳን ሰላማቸውን በመድፈር ልጆች አባት አልባ ፤ ትዳር አባወራ አልቦ እያሰቀረ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ልጆችህን ከባዕድ ጠላትህ ጋር እያደነ – እያሳደደ – እዬደበደበ – እያፈነ – እዬገደለ ነው ከቶ ይህ  ለአንተ ለጨዋውና ለአርቆ አሳቢው ዬኢትዮጵያ ህዝብ ተመችቶህ ይሆን? ስለምን ይሆን ሊይህ አብዝቶ የተጸዬፍህን፤ ሊያስጠጋህ የማያፈቅደውን አራዊት አቅፈህ የያዝከው?

ልጆችህ ዘመን ከሰጣቸው ሥልጣኔ ተጣቀሚ እንዳይሆኑ እግር ብረት ይጠብቃቸዋል? ለመሆኑ አሸባሪው ወያኔ ስለመሆኑ ጠንቅቀህ ትረዳዋለህን?! በዘርህ – በእምነትህ – በደምህ – እዬተነጠልክ የምተቀጠቀጥበት ዘመን እንዲያከትም የተመቻቸህለት ይህን የወረስከው ትውፊት ከዬት ይሆን? ለፍተህ አንጡራ ሃብትህን አፍሰህ የሠራህው ቤትህ እራሱ የአንተ አይደለም። ጣሪያና ግድግዳ ብቻ፤ ይህ የቁም ሞት ውርደት ነው እስኪ ከልብህ ሁነህ ግፉን አስላው?

እጅግ ዬምወድህ ክብሬ – የጥንት የጥዋቱ ነፃትነትህን በምን መልክ ነው ያገኘኸው? የወረስከው? በአርበኝነት እኮ ነው። አርበኝነት አሸባሪነት ተብሎ ሲፈረጅ ዝምታህ የትናንቱን የአባቶችህ ገደለ – ታምራት እንደ አጠቆርከው እስኪ አድምጠው። ታሪክን – ሀገርን – ቅርስን ውርስን – ባህልን ትውፊትን ማቆዬት አሸባሪ ሲባል ከዚህ የከረፋ ምን መራራ ነገር ከቶ ይጠበቃል?

ክብሬና ሞገሴ ናፍቆቴና ጌጤ የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! ሰንድቅዓላምህ እኮ እሰረኛ ነው። „ኢትዮጵያዊነትን“ ዬሚገልጹ ማናቸውም ነገሮች በአሻባሪነት የተመደቡ ናቸው። አንተም እራስህ የአርበኛው ውርስ ስለሆንክ በጫካው አውሬ በወያኔ በአሸባሪነት እንደተፈረጅክና ቀን ጠብቆም እዬለቀመ እንደሚቀጠቅጥህ በተደሞ መርምረው። የሚገዛህ የሚያስተዳድርህ ትናንት አከርካሪውን በዓለም አደባባይ ሰብረህ ቅጣቱን ሰጥተህ ያሰፈርከው የባንዳ መርህ ነው እያስፈጸመ ያለው።  በእጅ አዙር ዛሬ ቅኝ ሆነኃል። ይህ ለደምህ ይጥመው ይሆን?

የሴት እስረኛ ልጆች መከራ ደግሞ እጅግ እንቅልፍ የሚነሳ የሚያርመጠምጥ – ረመጥ ነው። ተገደው ነው በአካላቸው ለአጋዚ ሠራዊት መጫወቻ የሚሆኑት። ይህን የከረፋ ሥርዓት ከሥሩ ለመንቀል አታቅማማ አምላክህ ደግሞ ከግፉዕን ጋር ነውና ድምጽህን አሰማ – በአደባባይ!

ያ የጥንት ዬጥዋቱን ማንነትህን – አንተንህን የሰጠህን ቀና ብለህ እንደትሄድ ያደረገህ አንጡራ ጥሪትህ ተፈሪነትህ ሁሉ ወያኔ ጎርጉሮ – ዘርፎ  - አራቁቶ ግብዕታቸውን እዬፈጸመ ነው። እኮ የእኔ ጌጥ ሸክምህን ለማራገፍ መቼ ይሆን የምትቆርጠው? ከስሜን እሰከ ደቡብ፣ ከደቡብ እስከ ምስራቅ፤ ከምስራቅ እስከ ምዕራብ „አሻም መታረድ፣ አሻም መቀጥቀጥ አሻም መታሠር፣ አሻም መሰደድ አሻም ልጅ መቀማት“ ብለህ በቁርጥ ቀን ድምጽህን አጉልተህ ከአምላክህ ጋር ተባብረህ የምተነሳበት ቀን ከቶ መቼ ይሆን? እያረሩ ኑሮ ለአሻሮነት እንጂ ለነጠረው ኢትዮጵያነት ክብር አይመጥንምና ተነስ!

ኢትዮጵያዊነት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጥር!
ጀግኖቻችን ክብሮቻችን ናቸው!

እግዚአብሄር ይስጥልኝ!

No comments:

Post a Comment