Monday, October 27, 2014

የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል ላለፉት 3 ወራቶች ያሰለጠናቸውን የአምስተኛ ዙር ታጋዮች አስመረቀ!

በቅዱስ ዮሃንስ

አገራችን ኢትዮጵያ በጎጠኛውና በከፋፋዩ የፋሽስቱ ወያኔ አገዛዝ መዳፍ ውስጥ ከወደቀችበት ጊዜ ጀምሮ የደረሰባትንና እየደረሰባት ያለውን ውርደትና መከራ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በመገርሰስ ወደ ክብር ለመለወጥ፤ ብሎም የናቋትን እና ያዋረዷትን ጉጅሌዎች በፍትህ ሚዛን ላይ እንዲቀመጡና ፍርዳቸውን እንዲያገኙ ማድረግን ቀዳሚ አላማው አድርጎ ወደ ዱር የከተተውና፤ በአገራችን የነገሰውን ፍጹም አምባገነናዊ አገዛዝ በሚገባው ቋንቋ ሁሉ ለማነጋገር እጅግ በዘመነ ሁኔታ እየተደራጀ የሚገኘው የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል 5 ዙር ታጋዮችን ሰኞ ጥቅምት 17 ቀን 2007 አ.ም ማስመረቁን ከህዝባዊ ሃይሉ የተላከልን መረጃ ያመለክታል።ተመራቂ ታጋዮቹ ላለፉት 3 ወራት በተከታታይ በወታደራዊ፣ ፖለቲካዊ እና የመረጃ  እና  ደህንነት ትምህርቶች በበቂ ሁኔታ መሰልጠናቸው የተገለጸ ሲሆን በአሁኑ ሰአት ያለውን የሀገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበና ወቅቱ የሚፈልገውን ቴክኖሎጅ በመጠቀም መረጃን መቀበልና ማስተላለፍን የጨመረም እንደነበር ተያይዞ ተጠቅሷል።

በምረቃ  ስነስርዓቱ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የህዝባዊ ሃይሉ ዋና አዛዥ ኮማንደር አሰፋ ማሩ የህዝባዊ ሃይሉን ወቅታዊ አቋም በተመለከተ ሲናገሩ ‘’ህዝባዊ ሃይላችን በኢትዮጵያ ውስጥ የተንሰራፋውን ዘረኛና አፋኝ የወያኔ  አገዛዝ ከህዝባችንና ከአገራችን ጫንቃ  ላይ አስወግዶ በምትኩ ፍትሃዊ ና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት ከተመሰረተ ጀምሮ ባለፉት ጥቂት አመታት በርካታ  ስራዎችን  በመስራት አሁን አስተማማኝ  ድርጅታዊ አቋም ላይ  ይገኛል’’ ሲሉ በምረቃው ስነ ስርአት ላይ ለተገኙት የክብር እንግዶች ተናግረዋል። ኮማንደር አሰፋ ማሩ አያይዘው እንደገለጹት ‘’ይህን የአምስተኛ ዙር ምርቃት ከቀደምቶቹ 4 ዙር ምርቃቶች የሚለየው የኢትዮጲያ ህዝብ አርበኞች ግንባር፣ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ንቅናቄ እና የግንቦት ሰባት የፍትህ፣ የነጻነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ ተዋህደው ባንድ ድርጅታዊ ጥላ ስር ትግላቸውን አስተባብረው ለመታገል የሚያደርጉትን የውህደት ሂደት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ ያደረሱበት ወቅት ላይ መደረጉ ነው ‘’ ሲሉ አስረድተዋል። 

ኮማንደሩ በስተመጨረሻም ‘’ይህ የህዝባዊ ሃይላችን ስልጠና በግንቦት ሰባት ስም ከሚደረጉት ስልጠናዎች የመጨረሻው ይሆናል በማለት የገለጹ ሲሆን ለተመራቂ ታጋዮች ባስተላለፉት መልዕክት ‘’ስልጠና ላንድ ታጋይ የትግሉ  የመጀመሪያ  ምዕራፍ ሲሆን በስልጠና  ላይ ያገኛችሁትን  ትምህርት በተግባር ለቆምንለት ዓላማ  እና ተልዕኮ  በቁርጠኝነት  እንደምታውሉት ሙሉ እምነቴን እገልጻለሁ ‘’ ካሉ በኋላ  የአገርና የትውልድ ጠላት የሆነውን የፋሽስቱ ወያኔ አገዛዝን ከኢትዮጵያ ምድር ጠራርገን ለማስወገድ በምናደርገው እልህ አስጨረሽ ትግል አብረን እንቁም፤ ሕዝባዊ ሃይላችንንም ተቀላቀሉ ሲሉ ለኢትዮጵያ ህዝብ ወገናዊ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።


የግንቦት 7 ሕዝባዊ ሃይል በሀገር ውስጥ እንደማእበል እየገነፈለ ያለውን የአታግሉን የሕዝብ ጥያቄ በተደራጀና በተቀነባበረ መንገድ በተገቢው መልኩ ለማስተናገድ እንዲችል እንደ ድርጅት ከመቼው ጊዜ በላይ ራሱን እያደራጀና እያጠነከረ እንደሚገኝና ምቹ አታጋይ ተቋም ሆኖ ለመውጣት ሌት ተቀን እየደከመ የሚገኝ ድርጅት መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ከዚህ ቀደም በ 4 ተከታታይ ዙሮች በርካታ ታጋዮችን ማስመረቁን መዘገባችን አይዘነጋም። 



No comments:

Post a Comment